Monday 5 December 2011

‘እስከመቼ ፊትህን ታዞርብናለህ!’


ሰሞኑን በየድረ-ገጹ አበሾችን ወደየኮምፒውተር ሰሌዳቸው (ክትበ-ገበራቸው) እየገፋፋቸው ያለው በአገር ቤት ግብረ-ሰዶማውያን በኢትዮጵያ መንግሥት ድጋፍ ሊያደርጉት የተዘጋጁበት ስብሰባ ነው።

ስለዚህ ጉዳይ መጀመሪያ ያነበብኩት አዲስ-ሪፖርተር ባለፈው ዕሮብ ያወጣው ዘገባ ሲሆን፤ ይኼም የሃይማኖት አባቶች ጉዳዩን ለማውገዝ ያዘጋጁትን ውሳኔ ለጋዜጠኞች እንዳይስተላልፉ የጤና ጥበቃው ሚኒስትር ባልተገለጸ ምክንያትናዘዴ  እንዳስጣሏቸው ያበሰረው አንቀጹ ነው። ከዚኽ ቀጥሎ ያነበብኩት በዳንኤል ክብረት እይታዎች ላይእሳቱ ከሌለ ጢሱ አይታይምበሚል ርዕስ በዚያው ዕሮብ እለት ያሰፈረው መጣጥፍ ነው፡፡ ዳንኤል፣ ቅዳሜ ደግሞይህ ስም ክቡር ነው” በሚል ርዕስ ጠለቅ ያለ ዘገባ አስነበበን።

እነዚህ ትንተናዎች አያሌ አስተያየቶችን ስበዋል። አብዛኛዎቹ ተችዎች የዚህ ዜና አዎንታ ስሜታቸውን የቱን ያህል እንዳብሰለሰለውና እንዳሳረረው ከአጻጻፋቸው እንረዳለን። ግብረ-ሰዶማዊነት ከባህላችንም፣ ከሃይማኖታዊ እምነታችንም (በተለይ የኦርቶዶክስ ክርስትና) ጋራ የተጻረረ እና በጥብቅ የተከለከለ፤አስጸያፊ ድርጊት እንደሆነ እየደጋገሙ አስፍረውታል። አልፎ አልፎም ወቅታዊው የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግም ግብረ-ሰዶማዊነትን እንደሚከለክል ከነአንቀጹ በመጥቀስ ያስረዱንም አሉበት።

ዳንኤል “ኢትዮጵያ የሃይማኖት ሀገር ናት፡፡ ከ90 በመቶ በላይ የሆነው ሕዝቧ በእምነቱ ግብረ ሰዶምን ይቃወማል ብቻ ሳይሆን ይጸየፋል፡፡ የሀገሪቱ ሕጎችም ግብረ ሰዶማዊነትን በወንጀልነት ይፈርጃሉ፡፡ ከሕዝቡ እምነት ብቻ ሳይሆን ከባህሉ ጋርም የሚጣረስ ጉዳይ ነው፡፡” ብሎ እቅጩን ከነገረን በኋላ ከዚኽ ለጥቆም “ግብረሰዶማዊነትን ካልተቀበላችሁ፣ የግብረሰዶማውያንን መብት ካልደገፋችሁ አንረዳም እያሉ የሚያስፈራሩ ምዕራባውያን ኃያላን አሉ፡፡ ራሳችንን አጥተን የሚመጣ ርዳታ ለቀብር ማስፈጸሚያነት ብቻ የሚውል ነው፡፡ እናም እንዲቀርብን እንንገራቸው፡፡” በማለት የችግሩን መፍትሄ በከፊልም ቢሆን ሲጠቁም፤ ማንነታችንን እንወቅ፣ የሰፊውን ሕዝባችንን እምነትና ባህል የሚያረክሱ፣ የሚበክሉ፣ ባዕዳዊ ልምዶችን በስመ-ሥልጣኔ ወይም እርምጃ ለሣንቲም ብለን እየተቅበልን እራሳችንን አናዋርድ፣ አንግደል፣ አንቅበር እያለን ነው ያለው።

አንዱ ተች ደግሞ ምዕራገ ጸሎት፣ ዲቦ ቅድስት ድንግል ማርያም በምትባለው ገዳም ያሉ አባቶች በየዕለቱ በመላ አገሪቱ ውስጥ የተሰዋውን መስዋዕት የተጸለየውን ጸሎት እንደሚያሳርጉ ሲነግረን፤ እንዲህ ዓይነት ድርጊት የሚፈጸምባት ቅድስት ሃገር በተቃራኒው ርኩስ አስጸያፊ በሆነው በግብረ-ሰዶማዊነትም ስም አብራ መጠራት እንደሌለባት ሲይስታውሰን ሌላው ደግሞ (ስሙን እንኳን ያልነገረን ተቺ) የግል መብት ከሁሉም የበላይ እንደሆነና በግል ውሳኔ/ምርጫ ካቶሊክነት ወይም ኦርቶዶክሳዊነት ወይም እስልምና ወይም ሃይማኖተ-አልባ መሆን እንደምንችል ሁሉ፣ እንደግብረ-ሰዶማዊነትንም ያሉትን ተግባራት በግል መርጠን ማካሄድ መቻል መብታችን ነው ባይ ነው፡፡ ይኼኛው አስተያየት ሰጭ ታዲያ  ይፋ ከተደረጉት አስተያየቶች መኻል በጸረ ግብረ-ሰዶማውያን የተሰነዘሩት አስተያየቶች፣ ከሃይማኖት ወይም ከባህል ወይም ዝም ብሎ የመጥላት መንፈስ ውጭ ሌላ ምንም ዓይነት አስተያየት እንዳላየ ይተነትንና ሃይማኖታዊ የሆኑት ቅራኔዎች ለአማኞች ብቻ የሚሠሩ፤ ባህልን የተመረኮዙት ቅራኔዎች ደግሞ እንደማንኛውም ባህል ከጊዜ ሂደት ጋር እየተለወጡ መምጣት የማይቀርላቸው ናቸው ይለናል።

ታዲያ ይኼንን ሁሉ አንብቤ፤ እንደአብዛኛው ወገኔ እኔም በሀገሬ ላይ ያለኝ ተስፋ እየመነመነ፤ ውስጤ እየተቃጠለ፤ እንደኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ተከታይም፣ ወደፈጣሪ አምላኬም ‘እስከመቼ ፊትህን ታዞርብናለህ!’ ብዬ መጮኼም አልቀረም። የመንግሥት መገናኛ ብዙኃንስ በተለየ ስለዚህ የግብረ-ሰዶማውያን እንቅስቃሴም ኾነ ከፍተኛ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ ባለ-ሥልጣን የሃይማኖት አባቶች ላይ አደረጉ ስለተባለው ኢ-ዴሞክራሲያዊ የአፈና ተጽዕኖ ምን ብለው ይኾን ብዬ ብፈልግ፣ በሽምግልና በደከሙ ዓይኖቼ ስንፈት አልታይ ብለውኝ ካልኾነ በሰትቀር አንድም ነጥብ ላገኝ አልቻልኩም።

እኔን ታዲያ ወደዚህ ጽሑፍ የገፋፋኝ ይኼ ሁለተኛው አስተያየት ነው። በሃይማኖታዊ መሠረት የሚደነገግም ሆነ በዓለማዊ አስተዳደር በየጊዜው የሚተገበር ሕግ ሥር መሠረቱ የሚመነጨው ከተፈጥሮ ሕግጋትም መኾኑን መዘንጋት የለብንም። ለምሣሌ ያህል ይኼንን ጉዳይ የሚመለከተው የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ክፍል ሁለት ሲሆን ርዕሱ ‹‹ለተፈጥሮ ባሕርይ ተቃራኒ የሆነ የግብረ ሥጋ ግንኙነቶች›› ነው የሚለው። እንግዲህ በሰገላዊም ኾነ፤ ሃይማኖታዊ አገላለጽ ግብረ-ሰዶማዊነት “የተፈጥሮ ባሕርይ” ነው ብሎ  መሟገት ማለት በፍጡራን ውስጠ አካል፣ እንደ መተንፈስ፣ መመገብ እና የአካልን ብክነቶች የማስወገድ የመሳሰሉ ጠባያት ከንቁ-አዕምሮ ቁጥጥር ውጭ ለመራባት እና ራስን ከማጥፋት ለማዳን አብረውን የተፈጠሩ ግዴታዎች መሆናቸውን መካድ ነው። ሰው የተባለው ፍጡር ከተፈጥሮ ባሕርያቱ አንዱ ከተቃራኒ ፆታ ሰው ጋር ዘሩን የማርባት ግዴታውን ሟሟላት ከንቁ-አዕምሮ ውጭ የሚካሄድ ባሕርይ ነው። ይኼንን ደግሞ በግብረ-ሰዶማዊነት ማሟላት አይቻልም። አይ ግድ የለም! የግል መብት ስለሆነ ይፈቀድ ማለት ደግሞ ከተፈጥሮ ሕግ ጋር በመቃረን የሰው ልጅ ዘር ይጥፋ፤ እንዲጠፋም እናድርግ ማለት ነው።

በልጅነት ዘመኔ ባልንጀሮቼን የማታክትበት፤ እኔም ብሆን አሁን ከበሰልሁ በኋላ መለስ ብዬ ስገመግመው እኔውኑ የሚያሳፍረኝ አንድ ጠባይ ይዤ ነበረ። ደግነቱ እንደማንኛውም የልጅነት ጠባይ የጧት ጤዛ ሆኖ ነው የቀረው።  ለትንፋሻችን የምንጠቀመው ‘ኦክሲጂን’ የተባለው አየር በዓይናችን የማናየው፤ በእጃችን የማንዳስሰው ነገር ሆኖ፤ ዙሪያችንን ከቦ የሚገኝ እና ለመኖር የሚያስፈልጋቸው ፍጡራን ሁሉ የጋራ ንብረት ነው። በጎኑ ደግሞ ይኼን የጋራ ንብረት እኩል የመጠቀም መብት የያንዳንዱ ፍጡር ተፈጥሮአዊ መብት ሲሆን የባልንጀሮቼን ዓይን እስካልጠነቆልሁ ድረስ ዓይናቸው ስር ድረስ ጣቶቼን እያወናጨፍሁ በዓየር ላይ የመጠቀም መብቴን ካላሳመንኋችሁ እያልኩ አታክታቸው ነበረ። እውነትም የሰውን አካል እስካልነካን ድረስ (እንቅስቃሴያቸውን እየገታን እንኳ ቢሆንም) መብቴ በምንለው ነገር ሁሉ ላይ  እንዳሻን የመጠቀም መብት አለን ማለት በዚያ ባልበሰለ፣ ጨቅላ አዕምሮ አስተሳሰብ (በተለይም የጡንቻ ድጋፍ አለው ብለን ካመንን!) ማሳመን ይቻል ይሆናል። ነገር ግን የኔ አስተሳሰብ ጉድለቱ፤ መብት ማለት የሌላውን፤ ሃይማኖታዊም ይኹን ባህላዊ ወይም ተፈጥሮአዊ መብት እስካልነካ ድረስ ብቻ መሆኑን አለመገንዘብ ነበረ። እያንዳንዱ ፍጡር በሰውነቱ ዙሪያ እስከተወሰነ ርቀት ድረስ በዓይን የማይታይ፤ በእጅ የማይዳሰስ “የተፈጥሮ መንፈሱ (life-force) ወይም በባህላዊ ገለጻ፣ ውቃቢው የሚያስፈልገው ቦታ ሲወረርበት አይወድምም መብቱም እንደተነካበት ይቆጠራል።

እንግዲህ ለዚህ መጣጥፍ ያነሳሳኝ ሰው “የግል መብት ከሁሉም የበላይ ስለሆነ፣ እንደግብረ-ሰዶማዊነትንም ያሉትን ተግባራት በግል መርጠን ማካሄድ መቻል መብታችን ነው” ሲል ልክ እኔ በዚያ በርጥብ አስተሳሰቤ “ዓይንህን እስካልነካሁ ድረስ በዓየሩ ላይ ጣቶቼን ማወናጨፍ መብቴ ነው” እል እንደነበረው አይነት እጅግ የተዛባ እና ያልበሰለ አመለካከት ነው። በአሁኑ ጊዜ በየትኛውም ሕብረተ-ሰብ መገበያያ ተብሎ ጥቅም ላይ የሚገኘው በታተመ ወረቀት ወይም ከብረታ ብረት በተሠሩ ሣንቲሞች ነው። እኔም ሆንኩ ይኼ ወንድሜ ‘አይ እኔ መገበያየት የምፈልገው በአሞሌ ጨው ወይም አዝራር ነው” ማለት የግል መምረጥ መብታችን ቢሆንም ከሰው ፍጥረት ጋር እስካለን ድረስ የማይሠራ ባዶ-ቅል ኃሣብ ሆኖ እናገኘዋለን። ከኢትዮጵያ ሕብረተ-ሰብ ጋር ተቃራኒ የሆነ ተግባርንም በዚያ ሕብረተ-ሰብ መኻል የማካሄድ መብቴ ነው ማለትም እንደዚሁ ውዳሴ ከንቱ የኾነ አመለካከት ነው።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ከተፈጥሮ ግዴታዎች ተነስቶ በሃይማኖትም፤ በባህልም ሆነ በዘመናዊ አስተዳደር ሕግጋትን መሥርቶ በውዱ ሲተዳደርባቸው  እዚህ የደረሰ ሥልጡን ሕብረተ-ሰብ ነው። በሕብረተ-ሰብም ደረጃ ማሻሻልም ሆነ መለወጥ የሚያስፈልጋቸው ባህሎችም ሆኑ ልምዶች ቢኖሩትም ማንነቱን በማያዛባ እና ሁሉንም ወገን እኩል በሚጠቅም (ለዚያውም ተፈጥሮአዊ ግዴታን በማይቃረን መልኩ) እራሱ በራሱ ይለውጣቸዋል ወይም ያሻሽላቸዋል እንጂ ባዕድ ምዕራባውያን ባስቀመጡት መስፈርት ሊሆን አይችልም።

ይኼ እንግዲህ ‘የግል መብት’ በሚል አጠራር የምንመጻደቅባቸውን አዲስ ፈሊጦችን ሁሉ ያካትታል። አብሮም ልንረዳው የሚያስፈልገው ሌላው አዎንታ ደግሞ፤ በዴሞክራሲ ሥርዓት እንኳ ሕዝቡን የመምራትን ሥልጣን ጨብጠናል የሚሉት መሪዎችም ቢሆኑ የኢትዮጵያ ሕብረተ-ሰብ ተፈጥሮአዊንም ኾነ፤ እምነትን ወይም ባህልን ተመርኩዘው የተመሠረቱትን ሕግጋቱን በስሙ የማስከበር ሥልጣን እንጂ የመደምሰስ ወይም ሲደመሰስ ዝም ብሎ የማየት፤ የመለወጥ፤ የመጣስ ወይም የማስጣስ መብት የላቸውም። በዴሞክራሲ ሥርዓትም ሥልጣንን የጨበጡት ለኢትዮጵያውያን አገልግሎት እንጂ ለምዕራባውያን እያጎነበሱ ክብሩን ለማስገፈፍ እንዳልሆነ በፍጥነት ሊገነዘቡት ይገባቸዋል። አንዳንድ ነገሮች እጅግ አሰቃቂ፤ ነውር እና አይነኬ ናቸውና።

ኅዳር 25 ቀን 2004 ዓ/ም