Friday 13 May 2011

«ተጨናቂው የኢትዮጵያ አንበሳ»



በታኅሣሥ ወር ፲፱፻፶፫ ዓመተ ምሕረት የተከሰተው የነመንግሥቱ ነዋይ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የኢትዮጵያን ንጉዛት አናውጦት ካለፈ ዓመት ከሦስት ወር ሆኖታል። ጄኔራል መንግሥቱም በዚያው ምክንያት በስቅላት ከተገደሉ እነሆ ዓመት አለፋቸው። እቴጌ መነንም ከተለዩን ገና ሦስት ወራቸው ብቻ ነው። ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ብዙ የአፍሪቃ አገሮች ከአውሮፓውያን የቅኝ ግዛት ቀንበር ተላቀው የነፃነት እግራቸውን በዳዴ ለማጠናከር እየተፍጨረጨሩ ነው።

ታዲያ በዚያ ወቅት የአሜሪካው ‘ታይም’ መጽሔት ግንቦት ፳፬ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓመተ ምሕረት፤ «ተጨናቂው የኢትዮጵያ አንበሳ» በሚል ርዕስ ያወጣው ዓምድ ስሜቴን በተለያየ መልክ የፈተነ ጽሑፍ ነው። መቸም መራራ ሐቅን እቅጭ አድርገው ሲነግሩት የሚያሽረው ጥቂት ነውና። 

በመግቢያው አንቀጽ ላይ የአዲስ አበባ ሴት ዝሙት አዳሪዎች ማስተወቂያቸው “ቀይ መስቀል” ነበረ። ነገር ግን የዓለም አቀፍ የቀይ መስቀል ማኅበር መዝናናት የሚፈልጉ ብዙ ወንዶች እየተሳሳቱ በየክሊኒኮቼ ዘው እያሉ አስቸገሩኝ በማለቱ፤ እነኚህ ሴቶች ምልክታቸውን ወደ ቀይ መብራት እንዲለውጡ የመንግሥት ድንጋጌ መውጣቱን ያበሥራል። ታዲያ ይሄ ድንጋጌ ሥራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ የነኚህ የወንድ መዝናኛ ቤቶች ከአምስት ሺ ወደ ስምንት ሺ ማደጉንና የአካባቢው የመብራት ኃይል ፍጆታም ማሸቀቡን ይዘግባል።

ዛሬ ቢሆን “የኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት በእጥፍ አኃዝ ማደጉን የ’ታይም’ ጋዜጠኛ መሰከረ።” ነበር ርዕሰ አንቀጹ የሚለው።

 ‘ታይም’ እድገቱ የወቅቱን ለውጥ እንደሚያረጋግጥ ሲጠቁም፤ ምክንያቱንም ኢትዮጵያን የአፍሪቃ ነጻነት ትግል እምብርት ለማድረግ ንጉሠ ነገሥቱ የሚያደርጉት ጥረት በርዕሰ ከተማዋ በሚካሄዱት ሥፍር-የለሽ ስብሰባዎች ላይ ለመሳተፍ የሚጎርፉት እንግዶች ናቸው ይላል።  [ሌላው ቢቀር፣ ሽርሙጥና ከፍ ያለ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ሆነልን ማለቱ ይሆን? የትም ፍጪው፣ ዱቄቱን አምጪው! ይባል የለ?]

ወደታሪክ መለስ ብሎም «እነኚህ ዘራቸውን ከንጉሥ ሰሎሞንና ከንግሥት ሣባ በመምጣቱ የሚኮሩ
ኢትዮጵያውያን - ለብዙ ምዕት ዓመታት ጥቁር አፍሪቃውያንን “ባሪያ” እያሉ በማንቋሸሽ ኖረዋል።» ነገር ግን የጥቁር አፍሪቃ አገራት ነፃ እየወጡ ድምጻቸውን በዓለም መድረክ ላይ ማሰማት ከጀመሩ በኋላ ንጉሠ ነገሥቱ፣ ድሮ “ባርያ” እየተባሉ የሚናቁትን አሁን ግን «ተወዳጅ ጥቁር ወንድሞቻችን» በሚል ለአኅጉሩ መሪዎችና ታጋዮች የቅኝ-ግዛትን ሥርዓት በማውገዝ በደብዳቤ መልዕክቶቻቸውን ማብረር ጀመሩ። ካለ በኋላ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሰሞኑን በ ሦስት ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ($3,000,000) በተገነባው አዲሱ የ’አፍሪቃ አዳራሽ’ ውስጥ ተንቀሳቃሹን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የቅኝ  ግዛት ሸንጎ አባላትን እንደሚያስተናግዱ ይነግረናል። ከካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው አንዱ “ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደዚህ አይነት መስተንግዶ ለአፍሪቃ አኅጉር መሪነት ያላቸውን ምኞት እንደሚያሳካላቸው ያምናሉ” ይላል ።

ይኸው ኢትዮጵያዊ የካቢኔ ሚኒስቴር «እኛ ከሁሉም የቆየ ነፃነት አለን። በቅርብ ነፃነታቸውን የተቀዳጁትን ወንድሞቻችንን ደግሞ ወደዘመናዊው ዓለም የመምራት ግዴታችንም ቅርሳችንም ነው» ብሏል በሚል ጽሑፉን ያዘጋጀው የመጽሔቱ ቃል አቀባይ ጠቅሶታል። ታዲያ የጽሑፉ ደራሲ ጋዜጠኛ «ይቺ ከዓለም ኋላ ቀር አገሮች መኻል የምትሰለፍ አገር፤ ፓርላማዋ ሥራውም ሆነ ችሎታው የንጉሠ ነገሥቱን ፍጹም ሥልጣን በማኅተም መርገጫ የማጽደቅ ብቻ የሆነባት እና የመገናኛ ብዙሐን ነፃነት የማይከበርባት፤ ሰላዮችና ጆሮ ጠቢዎች በሰፊው የተሠማሩባት ኢትዮጵያ እንኳን ሌላ አገሮችን ወደዘመናዊው ዓለም ለመምራት ቀርቶ፣ እራሷም መንገዱ በየት እንደሆነ አይታውም አታውቅ።» በሚል ከእሳት ማዕበል የበለጠ በሚፋጁ ቃላቶቹ ሸንቁጦናል። የምታቦካው የላት የምትጋግረው አማራት አሉ አባቶቻችን!
ይሄ ብቻ መቼ በቃውና! ያ ብስለት የጎደለው፣ ጉረኛ [እንዲያውም ትዕቢት የተሞላበት ቃላቶች በመሰንዘሩም ‘አሳዳጊ የበደለው ባለጌ’] የካቢኔ ሚኒስቴር በሰነዘራቸው ቃላት መነሻነት ለጋዜጠኛው የስድብ ነጎድጓድ ዳርጎናል። ሞኝና ወረቀት የያዙትን አይለቁም እንደሚባለው ከልጅነቱ ጀምሮ ሲሰማው የቆየውን የስህተት አመለካከት ማረም እንኳ ያልቻለ ትሩማንትሪ!
መቸም በዚህ ጽሑፍ ላይ የሠፈሩትን ነጥቦች እውነተኛነት ላለመቀበል ሳይሆን፤ በባእድ ብዕር መሰደባችን እየከነከነኝ ነው። «ወንጀለኛ በአደባባይ የሚሰቀልበት አገር፣ ከነአካቴው የወህኒ ቤቶችን መጣበብ ለማቃለል እና ለ’እኔን አይተህ ተቀጣ’ም እንዲያመች በእሥራት ፋንታ በአደባባይ መገረፍ በቅርቡ ተፈቅዷል » ይልና፤ ስለሙስናም ሳይተርብ አያልፍም። በዘገባው እንዳሰፈረው ባለ ሥልጣናቱ በሙስና ከመጨማለቃቸው ብዛት ከሚሰበሰበው ቀረጥ ሲሦው ወደመንግሥት ካዝና አይገባም ብሏል።

የመንግሥቱ የአስተዳደር ብዛትና ክብደት ከአገሪቱ ዓመታዊ ወጭ ሁለት ሲሦውን ይበላዋል፤  በሀያ ሚሊዮን የሚገመተው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከአገሪቱ ሀብት የሚደርሰው በዓመት በአማካይ አምሥት የአሜሪካ ዶላር እንደሆነ፤ ከመቶ ሕዝብ ዘጠናው መሐይም፤ ሰማንያ በመቶው ደግሞ በጥገኛ ነፍሳት የተጠቃ፤ ገሚሱ የወሲብ በሽታ የተጸናወተው እና አርባ ከምቶ የሚሆኑ ሕጻናት እንደሚሞቱ፤ ወባ በየዓመቱ ሰላሳ ሺ ሰዎችን እንደሚገልና ከመቶ ከብቶች አርባዎቹ በሳምባ ነቀርሳ የተለከፉ እንደሆኑ ይተነትናል።

ኧረ በፈጠረህ ይበቃል! አልኩኝ ፣ አጠገቤ ያለ መስሎኝ!
እሱም «አንዴ ጀምሬዋለሁና በትእግሥት አስጨርሰኝ» የሚለኝ መሰለኝ። ለጥቆም «የነጮች ልምዳዊ ማሳጣት ነው፤ ይሄን ሁሉ የሚያስተነትንህ እያልከኝ አይደል? እሺ የኔንስ እንደዚያ ገምተው። ስብሰባ ላይ ሊሳተፍ የመጣውስ ጥቁር፤ አፍሪቃዊ፤ ሴኔጋላዊስ? ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?» ይለኛል። አያችሁ በታሪክ አውሎ ነፋስ እይተውዠገዠገ መጥቶ ልቦናዬን እንዴት እንደሚያስተኝ? ወቸ ጉድ!

ይሄ ሴኔጋላዊ የአዲስ አበባን አራት መቶ ሃምሣ ሺ ነዋሪዎች ድህነት፤ መራቆት እና  የኋላ ቀር ኑሮ ከተገነዘበ በኋላ “የነፃነት ውጤት ይሄ ከሆነ፤ መልሳችሁ ግዙኝ።” ብሎኛል አለ ጸሐፊው። ያ ምስኪን ሴኔጋላዊ ነፃነትን በቀመሰ በሁለት ዓመቱ እንኳንስ እኛን እንደመሪ ሊቆጥር ጭርሹንም የእኛ ኑሮ አቅለሽልሾት ነፃነቴ ይቅርብኝ እስከማለት መድረሱ ለጋዜጠኛው አመለካከት ድጋፍ እንደሰጠውና የዚያም የካቢኔ ሚኒስትር አጉል ድንፋታ ፍሬ-ቢስ እና ውዳሴ ከንቱ መሆኑን በማያሻማ መልክ አረጋግጦታል። ጉድ እኮ ነው!

ተንኮለኛው ዘጋቢማ ምን ዕዳ አለበት? «ይሄ ሁሉ [ኋላ ቀርነት] ለጞብኚ አፍሪቃውያን ምን ዓይነት አሉታዊ ስሜት እንደሚፈጥር የተገነዘቡት ንጉሠ ነገሥት»፣ ይላል አሜሪካዊው፤ «የኢንዱስትሪያዊ ልማት ከመጀመራቸውም ባሻገር ግድቦችን፤ ነዳጅ ማጣሪያ፤ ወደቦችን እና ፋብሪካዎችን ለማሠራት ከምዕራባውያንም ከምሥራቃውያንም ዕርዳታ እየተቀበሉ ነው።» ዳሩ ግን የራሳቸውን ሥልጣን ይቀንሱብኛል ብለው የሚያምኗቸውን የአስተዳደር እና የፓርላማ ማሻሻያ እርምጃዎችን ለመውሰድ አሻፈረኝ እንዳሉም አብሮ አስፍሯል። ከአሥራ ሰባት ወራት በፊት በንጉዛቱ ሥርዓት ላይ ተነስተው የነበሩት ምሑራን እና ተራማጅ ወገኖች፤ ምንም እንኳ የኃይለ ሥላሴ መንግሥት በሹመት፣ በሽልማት ሊደልላቸው ቢሞክርም እንቅስቃሴያቸው አልበረደም። ሆኖም እራሳቸውን በቅጡ ያላደራጁ እና ቀጣዩ የተቃውሞ እርምጃ ምን መሆን እንዳለበት ስላልተስማሙ ጩኸትና ጫጫታቸው አልተተገበረም።

የትንተናውን ድምዳሜ በንጉሠ ነገሥቱ ላይ በማተኮር፤ «የ፷፱ ዓመቱ ሽማግሌ በባለቤታቸው እና አራት ልጆቻቸው ሞት ብቸኛ ቢሆኑም እንኳ ከሃያ ስድስት ዓመታት በፊት በዓለም መንግሥታት ማኅበር መድረክ ላይ በመቆም ያሳዩት የጉልምስና ስሜት አሁንም አልራቃቸውም።» የ፵፭ ዓመት ዕድሜያቸውን የያዙት ልጃቸው አልጋ ወራሽ አስፋ ወሰን ግን ከአባትዬው ይልቅ የተራማጅነት አስተሳሰብ ያላቸው ቢሆኑም ባህሪያቸው ለስላሳ እና ጨፍጋጋ ነው ይልና፣ «የንጉሠ ነገሥቱ ዘውድ ሳይተላለፍ ብዙ የዘገየ እንደሆነ፤ በአሮጌው ሥርዓት ላይ ያለመው መሣሪያ ምላጭ መሳቡ የማይቀር ነው።» ሲል ዘገባውን ደምድሟል። ምከረው ምከረው እንቢ ካለ መከራ ይምከረው እንዲሉ፤ ጃንሆይም አልሰማ ብለው….

በሚቀጥለው የታሪክ አውሎ ነፋስ እስከምንገናኝ፤ የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ!


Wednesday 4 May 2011

የ፸ ዓመት ነፃነት

        ሚያዝያ ፳፯ ቀን አባቶቻችንና እናቶቻችን አርበኞች ግፈኛውን የፋሺስት ኢጣልያ ሠራዊት ድል ያደረጉበት ማስታወሻ አድርገን እናከብረዋለን። በ፳፻፫ ዓመተ ምሕረት፣ ነገ ደግሞ ርዕሰ ከተማችንን በከፊል ተረክበን፣ ሰንደቅ ዓላማችን የተውለበለበበት ሰባኛው ዓመት ማስታወሻ ስለሆነ ለየት ባለ ሁኔታ ለማክበር እንሞክራለን። ከነኛ ጀግኖች አርበኞቻችን መኸል መቸም በጊዜው ብዛት አብዛኛዎቹ ተለይተውን፣ የቀሩት ጥቂት ናቸው።

በዚህ የመታሰቢያ ጽሑፍ  ከዚህ ዕለት ጋር የተያያዙ ሦስት ዐቢይ ነጥቦችን ለማንሳት እፈልጋለሁ። እነዚህም፦

ሀ)      የዚህን ዕለት ‘የነፃነት ቀን’ ወይም ‘የድል በዓል’ መባል ትክክለነቱን፤
ለ)      ለድሉ ወይም ለነፃነቱ ላደረሱን ጥቂት፣ ተራፊ አባቶች እና እናቶች አርበኞቻችን ምን ውለታ ተደርጎላቸዋል?
ሐ)      እኛ ኢትዮጵያውያን ለ ፸ ዓመታት በጃችን ይዘነው የቆየነውን ‘ነፃነት’ እንደምን ተጠቅመንበታል?

ሀ)     የድል በዓል ሚያዝያ ፳፯ ወይስ ኅዳር ፲፱ ?

ንጉሠ ነገሥቱ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በምዕራብ ኢትዮጵያ ኡም ኢድላ (ኦሜድላ) ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ከተከሉበት ጥር ፲፪ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ/ም ጀምሮ በጎጃም እንጃባራ፤ ቡርዬ፣ ደምበጫ፣ ደብረ ማርቆስ አድርገው በእንጦጦ በር አዲስ አበባ እስከገቡ ድረስ፤ በአርበኞቻችን ኃይልና በእንግሊዝ ጦር ኃይሎች እርዳታ የጣሊያንን ኃይል እየደመሰሱ በሚጓዙበት ወቅት በምሥራቅና በደቡብ ምሥራቅ ኢትዮጵያ የነበሩት አርበኞችና የእንግሊዝ ሠራዊት እንደዚሁ በጅጅጋ፣ ሐረር፣ ድሬዳዋ፣ አዋሽ፣ ናዝሬትና ሞጆ አድርገው፣ ከፊታቸው የሚያጋጥማቸውን የፋሺስት ኃይል እየደመሰሱ ወደርዕሰ ከተማዋ ይገሰግሱ ነበር።

ታዲያ ከነኚህ ሁለት ግንባሮች ቀድሞ ከተማዋን መጋቢት ፳፰ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም ከጣሊያኖች የተረከበው እንግሊዛዊው ጄነራል ዌዘሮል ነበር።[1]  ንጉሠ ነገሥቱ እና ተከታዮቻቸው ከአንድ ወር በኋላ፣ ሚያዝያ ፳፯ ቀን አዲስ አበባን ተረከቡ።

በዚህ ጊዜ በደቡብ-ምዕራብ ኢትዮጵያ፤ ጅማ እስከ ግንቦት ፳፱ ድረስ በሰሜን ኢትዮጵያ ደግሞ ጎንደር እስከ ኅዳር ፲፱ ቀን ፲፱፻፴፬ ዓመተ ምሕረት ድረስ በጣሊያኖች እጅ ነበሩ።

እንግዲህ እንደምንገነዘበው 'ድል ቀን' ሚያዝያ  ፳፯ ቀን የሆነበት ዋናው እና ብቸኛው ምክንያት ንጉሠ ነገሥቱ አዲስ አበባ የገቡበት ዕለት ስለሆነ እንጂ መላዋ አገር ከፋሺስት ቀንበር የተላቀቀችበት ሆኖ አይደለም። ትክክለኛ ሆኖ መከበር ያለበት የጣሊያን ሠራዊት ለመጨረሻ እና ለዘለዓለም ሰንደቅ ዓላማውን ከኢትዮጵያ ምድር ያወረደበት እና ያለምንም ጥርጣሬ መሸነፉን አምኖ ጎንደር ላይ እጁን የሰጠበት ዕለት ኅዳር ፲፱ ቀን  ፲፱፻፴፬ ዓመተ ምሕረት መሆን ይገባዋል። 

ያለበለዚያማ በዚህ በመጨረሻው ግንባር ተሰማርተው ሲጋደሉ የቆዩትን አባቶቻችንን መስዋእትነት መዘንጋት፣ መደምሰስ ይሆንብናል። የእነ  ደጃዝማች ኪዳኔ ወልደመድኅን ደጃዝማች ሀብተ ሥላሴ በላይነህ ደጃዝማች በዛብህ በለው፣ ደጃዝማች ካሣ መሸሻ፣  ደጃዝማች ከበደ ወንድማገኝ፣ ፊታውራሪ ከበደ ካሣ፣ እና የሌሎችም ብዙ አባቶቻችን አፅም ይፋረደናል። ሌሎቹ አርበኞች፣ ስደተኞች ከአምሥት ዓመታት በኋላ ወደየዘመድ አዝማዳቸው፣ ወደየትውልድ አገራቸው ሲመለሱ፣ እነኚህ ግን ትጥቃቸውን ሳያወልቁ፣ ቅማል የወረረውን ጎፈሬያቸውን ሳይቆረጡ ወደሰሜን ዘመቻ ተሰማሩ። የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ከሚያዝያ ፴፫ እስከ ኅዳር ፴፬ ያሉትን ሰባት ወራት የደመሰሰባቸው ይበቃል።

'ድል በዓል' ዕለት መከበር ያለበት ሰንደቅ ዓላማ የተተከለበት ዕለት ከሆነ፣ እንግዲያውስ ኡም ኢድላ (ኦሜድላ) ላይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የትተከለበት ጥር ፲፪  ቀን ይከበራ! አይ፣ አዲስ አበባ ከፋሺስት ኢጣልያ እጅ የተፈለቀቀችበት ዕለት መሆን አለበት የተባለ እንደሆነ ደግሞ፣ እንግሊዛዊው ማጆር ጄኔራል ዌዘሮል ዋና ከተማዋን የተረከበበት መጋቢት ፳፰  ቀን ይሁና! የዚህኛው ቀን ችግር ግን ዌዘሮል ያውለበለበው የብሪታኒያን ሰንደቅ ዓላማ መሆኑ ነው።

እነዚህ ሁሉ የተለያዩ ቀናት እንድ ሚያዝያ ፳፯  'ድል' የሚለውን ቃል ሙሉ በሙሉ አርኪ በሆነ መልድ አያስተጋቡም። ኅዳር ፲፱ ቀን ግን የፋሺስትን ኃይል ከመላዋ ኢትዮጵያ ክልል አሽቀንጥረን አስውጥተን፣ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ዓላማችን በመላው አገራችን የተውለበለበበት፣ ራሳችንን በራሳችን የማስተዳደር መብታችን የተከብርበት ዕለት [የሰባት ዓመቱን የእንግሊዞችን ጣልቃ ገብነት ወደጎን ትተነው] በመሆኑ እውነተኛው "የድል ዕለት" ያደርገዋል።
ለ)     አርበኞች አባቶቻችን እና እናቶቻችን ስለስድስት ዓመት ተጋድሏቸው ምን ውለታ አገኙ?
        
ጠላት ኢትዮጵያን በወረረ ጊዜ አብዛኛዎቹ ተከላካይ ወገኖቻችን ዕድሜያቸው ከአሥራ ስምንት ዓመት እስከ ሃያ አንድ ዓመት ብቻ የነበሩ ወጣቶች ናቸው። አብዛኞቹ፣ የጦር መሪዎቻቸው፣ መኳንንቱ፣ መሣፍንቱ  ከነአካቴውም ንጉሠ ነገሥቱም ሳይቀሩ አጋፍጠዋቸው አገር ጥለው እግሬ አውጪኝ ሲበሩ፤ ሞትም እንኳ ቢመጣ ለጠላት አንገዛም ብለውት፤። ረሀብ ሲቆላቸው፣ ቅማል ደማቸውን ሲመጠምጥ፣ የመርዙ ጋዝ፣ የቦምባርዱ፣ የጥይቱ የተቅማጡ፣ እረ ምኑ-ቅጡ 

መንፈሰ ጠንካራ፣ አልበገር ባይ ባይሆኑማ ኖሮ እነሙሴ ቀስተኛን የመሰሉ ሰላዮች መኻላቸው እየገቡ፤ ‘ንጉሡ ጥሏት ለሄደው አገር ስለምን ትጉላላላችሁ? ኑ ግቡ፤ የኢጣልያ መንግሥት ይሾማችኋል፣ ይሸልማችኋል’ እያሉ አገራቸውን ሊያስከዷችእው ሞክረው አልነበረም?  ያ ትውልድ ግን ‘ለጥቅሜ ብዬ ውድ አገሬን፣ አለኝታዬን፣ መኩሪያዬን አሳልፌ አልሰጥም። ለነፃነቴ ብሞትም ክብሬ የዘለዓለም ነው።’ በሚል ጥብቅ እምነታቸው ተሰቃዩ፣ አጥንታቸውን በየሸንተረሩ ከሰከሱ፣ ደማቸው በየ ሸለቆው ፈሰሰ፤ እንደጥብቅነታቸው እንደ እምነታቸው ታዲያ ያንን መራራ ጠላት ከወሰን ድንበራቸው ለማባረር በቁ።

የዓፄ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት በነኚህ ኢትዮጵያውያን ደም ተመልሶ ሥልጣኑን ሲጨብጥ፣ እንደባለውለታ መንከባከብ፣ መሾም መሸለም፣ ማክበር ማስከበር ሲኖርበት፤ ከነአካቴው ውለታ ተቀባይነታቸው ቀርቶ እንደውለት መላሽ የትም ወድቀው እንዲቀሩ፣ ስማቸው እንዲጠፋ፣ ሥራ ስጡን ብለው በ’ደጅ ጥናት’ እንዲማቅቁ የሚጥር ሥርዓት ሆነባቸው። በስማቸው የተሠራውን የአራት ኪሎውን ሕንፃ እንኳን ለማስፈቀድ የነበረባቸውን እንግልት ይሄ ጸሐፊ በቅርብ ታዝቦታል። የኢትዮጵያ መንግሥት እነኚህን ባለውለታዎች፣ ሲሆን እስከ ጡረታ ዕድሜያቸው አገራቸውን እንዲያገለግሉ፤ ቢያንስ እንኳ ለዚያ ውለታቸው ክብራቸውን ጠብቆ በእንክብካቤ መጦር ሲገባው ነፍስ አውጪኝ የሸሹትን ስደተኞች ሲሾም ሲሸልም፣ እነኚህን ግን ከኢትዮጵያ ማዕድ ከልክሏቸው ኖረ።

በደርግ ዘመናት ደግሞ ጭርሱንም በትምህርት ቤት እንኳ ከአብዮቱ በፊት የነበረውን ታሪክ ወጣቱ እንዳይማረው ተከለከለ። ትንሽ መተዳደሪያ መሬት የነበራቸው ተነጠቁ። ወገን ለሌላቸው አርበኞች መርጃ ተብሎ የተሠራው የአራት ኪሎ ሕንፃቸው ሳይቀር ተወረሰ። መጦር የነበረባቸው የነፃነታችን ባለቤቶች እየለመኑ መኖር ግዴታ ሆነባቸው።[2]

ባለፉት ሃያ ዓመታትማ ብሶበታል። አንደኛ ቁጥራቸውም እያደር እየመነመነ ነው። ከሁሉም በላይ ግን የአሁኑም መንግሥት የነኚህን ባልውለታዎች ታሪክ ማንቋሸሽና ማጣጠል እንጂ ክብር መስጠትን የማያውቅ፤ ዘመኑ እንኳን ለሰማንያ፣ ዘጠና ዓመት አዛውንት ቀርቶ እየሠራ የሚበላው ወጣት ትውልድ ሊቋቋመው የማይችለው፣ ሽማግሌ ማክበር፣ መርዳት የነበረው የባህላችን ምሰሶ በሥልጣኔ፣ እድገትና እርምጃ ስም ሌት ተቀን በመጥረቢያ ስለት እንደሚከተከት ግንድ ሊወድቅ ምንም ያልቀረው ሆኗል። ታዲያ ለእነኚህ ባለውለታችን አዛውንት ምን ተስፋ አላቸው?

ሐ) የ፸ ዓመት ነፃነታችንን ምን ሠርተንበታል?
ከ፴፫ቱ ድል ጋር አብረው የገቡት እንግሊዞች ምሥጢራዊ ዓላማቸው ፋሺስት ኢጣልያን በቅኝ ገዥነት መተካት ኖሮ በስም የንግሊዝ ቅኝ ግዛት አንባል እንጂ በተግባር ግን እንደመዥገር ተጣብቀውብን ደማችንን ሲመጡ የኖሩባቸውን ሰባት ዓመታት ትተን በቀሩት ፷፫ ዓመታት ላይ ብናተኵር፤ ይሄንን ጥያቄ እንዴት ነው የምንመልሰው?
የዘውዱ ሥርዓት ከስደት እንደተመለሰ ሥልጣኑን በማጠናከር፣ ፈላጭ፣ ቆራጭ ሆኖ ፣የአምሥቱን ዓመታት ፍዳ ረስቶ/አስረስቶ ለሃያ ዓመታት ከገዛ በኋላ፤ የወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ቢደርግበትም የጭቆና ባሕሪውን አባባሰው እንጂ ለሕዝቡ ንቃት እና መሻሻል ምንም ይሄ ነው የሚባል ለውጥ አላመጣለትም። የዚያ የታኅሣሡ ሙከራ ግን በሕዝቡ ልቦና ላይ የጫረው የለውጥ እሳት ከ ፲፫ ዓመታት በኋላ ተፋፍሞ አሽቀንጥሮ ጣለው።
ተከታዩ አብዮት፣ ሕዝቡ እንደተመኘው፣ እንዳለመው የዴሞክራሲያ ውጤትን ሳይሆን የተጎናጸፈው፤ ጭርሹንም ከመቶ ዓመት በላይ ወደኋላ የገፈተረው ሥርዓት ሆነ። የሕዝብን ሉዐላዊነት፣ የሕግን የበላይነት፣ እኩልነትን፣ በኢትዮጵያዊነት ታሪክ ላይ የተመሠረተ ሥልጣኔን የሚሻ ሕዝብ ከነአካቴው ከጨካኞች የባሰ ጨካኝ፤ ከዲያብሎስ የበለጠ አረመኔ የአምባ ገነን ተገዢ አደረገው። በዲሞክራሲያ ፋንታ ለስድብ፣ ለውርደት፣ ለሞት ተዳረገ። የኢትዮጵያዊነት ወኔውን ተሰለበ።
ደሞ ያንን አሰቃቂ እና ፍሬ ቢስ ዘመን ከ፲፯ ዓመታት በኋላ ተገላገልኩ ሲል፤ ለባሰ ሥርዓት ከተዳረገ እነሆ ሀያ ዓመቱ ሆነ። ተለያይቶ የማያቀውን አንድ ሕዝብ በዘር አከፋፍሎ፣ አገርን በጉልበት ለመንጠቅ ለብዙ መቶ ዓመታት ሞክረው ያቃታቸውን ባዕዳውያንን በይፋ እየቆረሰ ‘ኑ ውሰዱልኝ’የሚል፣ የበላዩ ሊሆን የሚገባውን ሰፊውን የኢትዮጵያ ሕዝብ መብቱን ገፎ የሚገዛ የጉድ ጉድ፣ መዓት አናታችን ላይ ተመቻችቶ ቁጭ እንዲል ፈቀድንለት።
ዳግማዊ ምኒልክ የዛሬ መቶ ዓመት፣ ዕለተ ሞታቸው ሲቃረብ፤ ሕዝባቸውን እንዲህ ብለው መክረው ነበር፦

«እናንተ አንድ ልብ ከሆናችሁ በምቀኝነት እርስ በርሳችሁ ተዋግታችሁ ካላለቃችሁ በቀር ኢትዮጵያን አገራችንን ለሌላ ለባዕድ አትሰጧትም፤ ክፉም ነገር አገራችንን አያገኛትም። ነፋስ እንዳይገባባችሁ አገራችሁን በያላችሁበት በርትታችሁ ጠብቁ፤ ወንድሜ ወንድሜ እየተባባላችሁ ተደጋገፉ፤ የኢትዮጵያን ጠላት ተጋግዛችሁ ተድንበር መልሱ። የኢትዮጵያ ጠላት ባንዱ ወገን ትቶ ባንድ ወገን ቢሄድና ድንበር ቢገፋ፤ በኔ ወገን ታልመጣ ምን ቸገረኝ ብላችሁ ዝም አትበሉ፤ ያ ጠላት በመጣበት በኩል ኁላችሁም ሄዳችሁ አንድነት ተጋግዛችሁ ጠላታችሁን መልሱ እስከ እየቤታችሁ እስኪመጣ ዝም ብላችሁ አትቆዩ»
 ይሄ ቃላቸው በታሪክ አውሎ ነፋስ ተምዠግዥጎ እኛም ዦሮ ሲገባ፣ መልእክቱ ለዘመናቸው ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለኛም፤ ለመጪውም ትውልድ እንደሆነ እንገነዘባለን። በዛሬው የመከፋፈል፣ የዘረኛነት እና መንፈሰ ደካማ ሥርዓት ግን ምኒልክ ከነአካቴው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት ተብለው ተወነጀሉ።
በበኩሌ ያንን ሁሉ መሥዋዕትነት፣ ያንን ሁሉ ተጋድሎ አባክነነዋል እላለሁ እንጂ የ፸ ዓመት ነፃነታችንን በአግባቡ ተጠቅመንበትም ለወደፊቱም ትውልድ ቋሚ ነገር ለማሸጋገር በቅተናል አልልም።

የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ
[ሚያዝያ ፳፮ ቀን ፳፻፫ ዓ/ም]





[1] The Abyssinian Campaigns, Issued for the War Office by the Ministry of Information (1942)

Monday 2 May 2011

የጃንሆይ ወርቅ


በየካቲት ወር የፈነዳው ሥር-ሰደድ ነውጥ የጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድን መንግሥት ፈንቅሎ ከጣለ አራተኛ ወሩን ይዟል። የልጅ እንዳልካቸው መኮንን ካቢኔ አገሪቱን የሚያስተዳድረው  መቸም ያው በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ስም ቢሆንም፣ የሥልጣን ገመዱን የሚያሥር የሚፈታው፤ የሚያጠብቅ የሚያላላው ግን ወታደራዊው ደርግ ነው። አብዮቱ ከሰሜን እስከ ደቡብ፤ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ በመላ ኢትዮጵያ ተፋፍሟል።

የአብዮቱን መርሐ-ግብር ተከትሎ የልጅ እንዳልካቸው መንግሥት አዲስ ሕገ መንግሥት የሚያዘጋጅ ሸንጎ እና የቀድሞዎቹንም ሆነ የወቅቱን ባለ ሥልጣናት፤ መኳንንት እና የዘውድ ቤተሰቦችን የአስተዳደር  ወንጀል እና ሙስና የሚያጠናም ሸንጎ ተቋቁሞ በየዕለቱ ብዙዎቹ ለወህኒ እየተዳረጉ ነው። የልጅ እንዳልካቸውም መንግሥት በተራው ሊወድቅ አንድ ወር ያህል ነው የቀረው።

ታዲያ በወቅቱ በኢትዮጵያ የብሪታኒያ አምባሳዶር የነበረው ዊሊ ሞሪስ (Sir Willie Morris, K.C.M.G.)  የየዕለቱን ዜና፤ ከእንደነ ኮሞዶር እስክንድር ደስታ፣ ልዑል ራስ አሥራተ ካሣ እና ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ የሚያገኘውን መረጃዎች፤ ወ.ዘ.ተ. ከራሱ ምርመራና አስተያየት ጋር እያጣመረ ወደሀገሩ የላካቸው እጅግ ብዙ ሰነዶች በብሪታኒያ ብሔራዊ መዝገብ ቤት (Public Records Office) ይገኛሉ።

ከእነኚህ ዶሴዎች መሀል ፤ ‘የኢትዮጵያ ሕዝብ በዘውዱ ሥርዓት ባለሥልጣናትና ንጉሣውያን ቤተሰቦች ተበዝብዟል’ በሚባልበትና  ‘በወሎ ሕዝብ የረሀብ ስቃይ’ ዓለም ባዘነበት በዚያ ቀውጢ ወቅት፤ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ልዩ በረራ ተጭኖ በድብቅ ወደ ሎንዶን ስለተላከ ወርቅ የተጻፉ ትንታኔዎችና ማስታወሻዎች ናቸው።

አምባሳዶር ዊሊ ሞሪስ ፣ ሰኔ ፳፬ ቀን ፲፱፻፷፮ ዓ/ም ወደሎንዶን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በላከው ቴሌግራም (አ/አ ቴሌ 304) ላይ፦

«የኢትዮጵያ አየር መንግድ ድርጅት ውስጥ ካለው ምንጫችን እንደተረዳነው ሰኞ ሰኔ ፲፯ ቀን ፲፱፻፷፮ ዓ/ም  በቤተ መንግሥቱ የግል ኮንትራት፤  አራት መቶ ስልሳ ሰባት  ሣጥኖች ጭኖ ነዳጅ ለመሙላት አቴና ላይ ካረፈ በኋላ ወደሎንዶን ተጉዟል።» ይልና፣ «ጭነቱ በሙሉ ወርቅ እንደሆነ ገምተናል። የዚህን ምንጭ እውነተኛነት ማወቅ ስለምንፈልግ፤ እውን ልዩ በረራ በተባለው ቀን ሎንዶን ገብቶ እንደሆነ፤  ገብቶም ከሆነ በአስተያየታችን የብሔራዊ ባንኩ የተለምዶ ተልዕኮ ስለማይመስለን የጭነቱን ዓይነት እና ተቀባዩ ማን እንደሆነ እንድታረጋግጡ እናሳስባለን።»

ይሄ የአዲስ አበባው ቴሌግራም እንደደረሰ፣ በብሪታኒያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ የምሥራቅ አፍሪቃ ክፍል ኃላፊዎች ጉዳዩ እንዲጣራ ያዛሉ። ውጤቱም ከብሪታኒያ የንግድ ሚኒስቴር እና ከጉምሩክ የመነጨ መረጃ ሲሆን የምሥራቅ አፍሪቃ ክፍሉ ፦

፩ኛ) በሰኔ ፲፮  እና ፲፯ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁለት ልዩ በረራዎችን ፈጽሟል።
ሀ) አንደኛው በዠኔቭ በኩል አድርጎ ሎንዶን ሰኔ ፲፮ ቀን ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ግድም የገባው ሲሆን
ለ) ሁለተኛው ደግሞ ‘የጭነት ብቻ’ በረራ ሲሆን በአቴና በኩል አድርጎ ሎንዶን በማግሥቱ ከጧቱ አንድ  ሰዓት ከሩብ ላይ አርፏል።
፪ኛ) ሁለተኛው በረራ የያዘው ጭነት “ውድ ዕቃ” የሚል መግለጫ የያዘ በመሆኑ በጉምሩክ አልተከፈተምም፣ ቀረጥም ያስከፍላል ተብሎ አልተገመተም። ጭነቱ አምባሳደሩ እንዳለው አራት መቶ ስልሳ ሰባት  ሣጥኖች ብቻ ሳይሆን፣ ፮፻፴፪ ሣጥኖችን ያጠቃለለ ሲሆን ጠቅላላ ሚዛኑ ፲፬  ፯መቶ ፹፱ ኪሎ ነው። ጭነቱ በሙሉ ይሄንኑ ሊያጓጉዝ ለተኮናተረው ኩባንያ ተላልፏል።

በጉምሩክ በኩል ደግሞ የቀረበው ጥቆማ ፦ በአየር ዠበብ ማረፊያው የጉምሩክ ምክትል ሀላፊ፣ በድብቅ ይሄን ጉዳይ ከመረመረ በኋላ፤ የገቡት ሣጥኖች ፮፻፴፪  እንደሆኑና በውስጣቸው ዋጋው በ፳፮ ሚሊዮን ፮፻፴፭ ሺ ፫፻፸፰  የእንግሊዝ ፓውንድ (£26,635,378.25)የተገመተ ያልተጣራ ወርቅ እንደሆነ እና በጠቅላላው ሚዛኑ ፲፬ ሺ ፻፴፬ ኪሎ ከ ፭፻፸፮ ግራም መሆኑን፣  ይሄውም የወርቅ ጭነት የተላከው በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ስም ወደእንግሊዝ ብሔራዊ ባንክ እንዲገባ ነው። 

በንግድ ሚኒስቴር [ግምት] ሚዛን እና በጉምሩኩ ሚዛን መኻል የክብደት ቅራኔ መነሳቱን አንባቢ ልብ ይሏል። የጎደለው ፮፻፶፬ ኪሎ ወርቅ ምን ሆኖ ይሆን? የመጀመሪያው ዘገባ ተሳስቶ ነው ወይስ ያልተገለጸ የ ፩ ሚሊዮን ፪፻፴፫ ሺ ፓውንድ (በእንግሊዞቹ ተመን!) (ቀረጥ?/ዝርፊያ?) ተቀንሶ ነው?

የንግድ ሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ “ጭነቱ ‘ውድ ዕቃ’ የሚል መግለጫ በመያዙ ብቻ ጉምሩክ ሳይከፍት/ሳይመረምር፤ የቀረጥም ተመን ሳያሰላ እንዲያው በደፈናው ለአጓጓዡ ወኪል አስረከበ ሲለን ልናምነው እንችላለን? ‘ውድ ዕቃ’ ከማለት ‘የዲፕሎማቲክ ጭነት’ የሚል ነበር ቢለን እንኳ ያለመፈተሹ ባላስገረመንም ነበር። ዞሮ ዞሮ ያልከፈቱትን ጭነት ምንነት ከነ ሚዛኑ እና ከነግምት ዋጋው ሊያውቁ የቻሉበትን ዘዴ አንባቢ  የራሱን ግምትና ትርጉም ሊሰጠው ይችላል።

ሌላው ደግሞ በዚህ ዶሴ ውስጥ በዠኔቭ በኩል ሎንዶን ገባ የተባለው የአየር መንገዱ ያልታሰበ በረራ ጉዳይ መካተቱ ትርጉሙ ምንድነው? ዠኔቭም የአየር መንገዱ ቋሚ መሥመር ስላልነበረ፣ ለምንድነው ወደዠኔቭስ የተላከው? ሌላ የ“ውድ ዕቃ” ጭነት ወደዠኔቭም ትልኮ ይሆን?

ሆኖም  የብሪታኒያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከአዲስ አበባ የተላለፈላቸውን መልዕክት ተከታትለናል ብለው በጊዜው የመሥሪያ ቤቱ ሚኒስትር በነበሩት፤ ጄምስ ካላሃን (በኋላ የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር) ስም ወደ አዲስ አበባው  አምባሳዶር  ይሄንኑ ‘መረጃ’ የተመረኮዘ መልእክት (የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቴሌ 268)[i] ሲያስተላልፉ፣ የምሥራቅ አፍሪቃ ክፍል ባልደረባ፤ ሪቻርድ ጎዝኒ (Sir Richard Hugh Turton Gozney) ግን ምናልባት ወደፊት ለሚነሳ ጥያቄ በሚል ሰኔ ፳፰ ቀን ፲፱፻፷፮ ዓ/ም በጻፈው የመዝገብ ማስታወሻ ላይ:-

«… በሕግ ድንጋጌው መሠረት በብሪታኒያ ክልል ውስጥ ያጓጓዙበትን የሰነድ ቅርጽ ለሁለት ዓመት ማስቀመጥ ግዴታቸው ስለሆነ…» ይልና የአጓጓዡን አድራሻ ከዶሴው ጋር አያይዞ አስቀምጦታል። ይሄ ጉዳይ በዶሴው ላይ እንደገና የሚነሳው በአዲስ አበባው ኤምባሲ የፖለቲካ  ክፍል ኃላፊ, ኢያን መሪ (Iain Murray)  ነሐሴ ፳፰ ቀን ለምሥራቅ አፍሪቃ ክፍል ባስተላለፈውበምስጢር የሚያዝ ሰነድ” ላይ ነው።

በዚህ ሰነድ ላይ፣ በጊዜው ለእንግሊዞቹ [ለአሜሪካኖቹም] በምስጢር ቃል ያቀብላቸው ከነበረው አቶ ሳሙኤል ዓለማየሁ [በአፍሪቃ አንድነት ድርጅት የቅኝ ግዛቶች ጉዳይ ክፍል የኢትዮጵያ ዋና ተወካይ] ጋር የተደረገውን ውይይት በመጥቀስ የቀረበው የኢያን መሪ ዘገባ፦
<<ሳሙኤል የዚያን ወደ እንግሊዝ ብሔራዊ ባንክ የተላከውን የወርቅ ጉዳይ ዛሬም አነሳብኝ። በአብዮተኞች መኻል የተፋፋመ ውይይት እየተካሄደ መሆኑንና የብሪታኒያ መንግሥት ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አጋር ነው እየተባለ ነው። ወርቁን በድብቅ ከአገር ያሸሹት መሆኑን እያወቁ አደራ መቀበላቸው፤  በተለይም በቅርቡ ከ’ቶማስ ደላሩ ኩባንያ’ አዲስ የታተመ የኢትዮጵያ ገንዘብ መላኩ ንጉሠ ነገሥቱ ተቃራኒዎቻቸውን እንዲገዙበት ሆን ብሎ የተላከ ነው።>> እያሉ እንደሆነ የሚወያዩት ነገረኝ ሲል ጽፏል።[ii]

ታዲያ ወዲያው ንጉሠ ነገሥቱ ከሥልጣን ሊወርዱ አንድ ቀን ሲቀር፣ ከአዲስ አበባ በተላከ ደብዳቤ፣ የዚህ የወርቅ ጉዳይ በመላው አዲስ አበባ ይፋ መሆኑንና ብዙ ውዝግብ እያስከተለ መሆኑን ይገልጽና የብሪታኒያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሁንም ጠለቅ አድርጎ ጉዳዩን እንዲመረምር፣ በተለይም «በእንግሊዝ ብሔራዊ ባንክ፣ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ስም የሒሣብ ደብተር አንድ ብቻ ነው? ወይስ ሌሎችም አሉ? ይሄ ወርቅ የገባበት የሒሣብ ደብተርስ በማን ቁጥጥር ስር ነው?» የሚሉትን ጥያቄዎች እንዲያጣሩለትና እንዲያስታውቁት ያሳስባል። ቀጥሎም በአዲስ ተገኘ በሚለው መረጃ መሠረት፣ ወርቁ በመጋቢት ወር ላይ በጊዜው የገንዘብ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ማሞ ታደሰ ‘ባልሆኑ ሰዎች እጅ እንዳይገባ' [ዘውዳዊ ቤተሰቦች ማልታቸው ይሆን?]በሚል ከገንዘብ ሚኒስቴር ካዝና አውጥተው ወደብሔራዊ ባንክ አዛወሩት። በሰኔ ወር በድብቅ ወደእንግሊዝ አገር ሲጫን ይዘውት የሄዱት ምክትል ሚኒስትሩ በጅሮንድ ገዛኸኝ ገብረ-ማርያም እንደሆኑ ይነግረናል።

የዚህ ደብዳቤ ጥያቄዎች የምሥራቅ አፍሪቃ ክፍል ኃላፊዎችን እንደገና አነቃቅቷቸው፣ ለእንግሊዝ ብሔራዊ ባንክ ጥያቄያቸውን አቀረቡ። የባንኩ ተወካይ መስከረም ፲፬ ቀን ፲፱፻፷፯ ዓ/ም በተጻፈ ደብዳቤ መልስ ሲሰጥ፣ እንደዚህ ያለውን በሁለት ብሔራዊ ባንኮች መካከል ያለ የሥራ ይዘት ምሥጢራዊ ጉዳይ መሆኑን፤ አሁንም ስለዚህ ምስጢራዊ ጉዳይ ለመጻፍ የተገደደው በአዲስ አበባ የብሪታኒያ ተልዕኮ አለአግባብ የሚሰነዘሩበትን ጥያቄዎች ለመመከት ይረዳዋል በሚል መሆኑን ካስረገጠ በኋላ የተላከው ያልተጣራ ወርቅ በተለመደ ሥርዓት መሆኑን እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አልፎ አልፎ እንደዚሁ ያልተጣራ ወርቅ እየላከላቸው እነሱ በወኪልነት ወርቁን አጣርተው በጡብ መልክ መልሰው በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የሒሣብ ደብተር ውስጥ ማስገባት የተለመደ ሥራቸው እንደሆነ በማስረዳት ደምድሞታል።

እንግዲህ የዚህን ወርቅ ጉዳይ በተመለከተ፤ ጸሓፊው ከብሪታኒያ መዝገብ ቤት ያገኘው ይሄው ነው። በዚሁ መዝገብ ቤት ከአሁን በፊትም በጣሊያን ወረራ ጊዜ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወደስደት ሲጓዙ ጠገራ ብር እና ብዙ ወርቅ ጭነው ስለመሄዳቸው የተጻፉ ሰነዶች አሉ። ዳሩ ግን በመኻላቸው ሰላሳ ስምንት ዓመታት ያለፉ ቢሆንም፤ በተመሳሳይነታቸው እና ለንብረቱ ባለቤት የኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም አይነት እርካታ የሚሰጥ እልባት ላይ ያልደረሱ ጉዳዮች ስለሆኑ መቸም ይሄን በሚያነቡ ኢትዮጵያውያን አዕምሮ ውስጥ እጅግ ብዙ ጥያቄዎችን እንደሚጭር አልጠራጠርም። ወርቁ ተመልሶ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በኩል ለኢትዮጵያ ጥቅም ውሎ ይሆን? ወይስ እንዲያው ተደባብሶ ቀልጦ የቀረ ጉዳይ ይሆን?

የእንግሊዝ ብሔራዊ ባንክስ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ልዩ ልዩ የሒሣብ ደብተሮች አሉት ወይ? ይሄ ወርቅ የገባበትንስ ደብተር የሚቆጣጠረው (ሒሣብ የማስገባት የማስወጣት ሥልጣን) ማነው? በሚል የቀረቡለትን ጥያቄዎች በዝምታ ማለፉ ለምን ይሆን? 
ከዚህ ታሪክስ አንጻር የአሁኒቱ ኢትዮጵያ ምን ተምራበታለች? የሕዝብን ንብረት በስሙ ሲንቀሳቀስ ሕጋዊ እና ግልጽ ለመሆኑ ዋስትናው ምንድነው? ወይስ 'ይሄ ያለፈ፣ ያከተመ ጉዳይ አይመለከተንም' ተብሎ ይታለፋል? ነጮቹ ከዚህ እንደምናየው የሚመለከታቸውንም ሆነ በቀጥታ የማይመለከታቸውንም ቢሆን በጥንቃቄ  በማስቀመጥ የአስተዳደራቸውን ግልጽነት መተማመኛ ዋስትና፤ የዜጎቻቸው የማወቅ መብት  ከመሆኑም በተረፈ ለታሪክ ትምህርትም ሆነ ለማንነታቸው ዋና ምንጭ የሆነ  መዝገብ ቤት አላቸው።

መቸም አንባቢያን፣ ሌላ መረጃም ሆነ ወይም ለተነሱትም/ሊነሱም ለሚችሉ ጥያቄዎች አስተያየት ካለ እንደሚያካፍሉን ተስፋ አደርጋለሁ።

በሌላ ‘የታሪክ አውሎ ነፋስ’ ዓምድ እስከምንገናኝ፤ የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ ሰላም ቆዩ!


ዋቢ ምንጭ፡ P.R.O., FO 31/1661; FO 31/1668



[i] F C O telegram to Addis Ababa #268; 3 July, 1974
[ii] Murray, Iain [AA] to Rosalind MacKechnie [FCO EAD] dated 3rd September, 1974