Showing posts with label Ethiopia: Blast from the Past. Show all posts
Showing posts with label Ethiopia: Blast from the Past. Show all posts

Thursday 27 June 2013

ሚካኤል (ወልቃይቴ) ብሩ እና ዳውቲ-ዋይሊ

ሚካኤል (ወልቃይቴ) ብሩ እና ዳውቲ-ዋይሊ
የብሪታኒያው ዋና መላክተኛና ባልደረባዎቹ አዲስ አበባ ላይ የተደበደቡ ዕለት።

ዚህ ትረካ ደራሲ ከዚህ በፊት “የየዋሖቹ ዘመን” ባልኩት ጽሑፌ መተዋወቃችንን ለማስትወስ ያህል፤ በዕምዬ ምኒልክ ዘመን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በቅሎው እሰው ማሳ ውስጥ ይገባና የአቅሙን ያህል የጤፍ እሸት አጋበሶ ከዋጠ በኋላ የተፈጥሮው ግዳጅ ቢሆንበት፣ በቀረው ሰብል ላይ እየተንከባለለ መዥገር ማላቀቂያ አድርጎ ያወድመዋል። ኦሮምኛ ተናጋሪው የማሳው ባለቤት  ታዲያ የካሣውን አሞሌ ጨው ቢጠይቅ የቋንቋ አለመግባባት ሆነና፤ ከማሳው ጠቅላላ ምርት ግምት በላይ ከአንድ ብር ሁለት ብር፤ ሦስት ብር፣ አራት ብር ቢከፈለው  ጊዜ በቅሎውን እንደልቡ እንዲሰድበት መነገሩን ያጫወተን ሻለቃ ሄንሪ ዳርሊ መሆኑን ከወዲሁ አንባቢ ይገንዘብልኝ!

Monday 24 June 2013

የኢትዮጵያ የአበባ ምርት በአፍጋኒስታን ገበያ አገኘ እንዴ ?

ይመኩ ታምራት (ከሎንዶን)

ሰኞ ሰኔ 17 ቀን 2005 ዓ/ም

ሐቅ! የአየር መንገዳችን የጭነት ጥያራዎች በግንቦት እና በያዝነው ሰኔ ወራት ወደ አፍጋኒስታን ደፋ ቀና ሲሉ ታይተዋል። (Flight Radar24.com ድረ-ገጽን ይመልከቱ)

ሐቅ! አየር መንገዱ ስድስት የጭነት ጥያራዎችን አሰማርቶ በቋሚ መልክ ወደ አውሮፓ፤ መካከለኛው ምሥራቅ እና እስያ ሸቀጣ
ሸቀጥ ያመላልሳል። ኾኖም አፍጋኒስታን በቋሚነት ከሚበርባቸው አገሮች መኻል ያልተመዘገበች ከመሆኗም ባሻገር በጦርነት ከተዘፈቀች አገር ጋር ምን ዓይነት ንግድ ተጀመሮ ይሆን የሚያስብሉ ሰባት በረራዎች ቀልቤን ሊስቡት ችለዋል።

ሐቅ!  አፍጋኖቹ ያለፉትን ሦስት-አሥርት ያህል ዓመታት ያሳለፉት እርስ በርስ በመፋጀት፤ በመፈራረቅ አገራቸውን የያዙባቸውን የሁለቱን ኃያላን መንግሥታት ወራሪ ሠራዊቶች በመከላከል እና በመኻሉም አክራሪ-ሃይማኖተኝነትን መርኅ በማድረግ ነው። የአገራቸው መልክዓ-ምድር እንደ ኢትዮጵያ ተራራማ ከመኾኑም ባሻገር የገጠሩ ዜጋ አኗኗር የኛውኑ ገጠሬ ጋር ይመሳሰላል። በጎቻቸው እንኳ በላት ምትክ ቂጣሞች ይሁኑ እንጂ የኛውኑ የአዳል ሙክት ነው የሚመስሉት።  ግን ከኋላቸው ሲያስጠ................ሉ!!

Wednesday 19 June 2013

የቡድን ስምንት ወጥ ቀማሽ

«የቡድን ስምንት መሪዎች መለስ ዜናዊን የሚተካ ወጥ ቀማሽ እያፈላለጉ ነው» ተባለ።

ይመኩ ታምራት

ከአዲስ አበባ ዕሮብ ሰኔ ፭ ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ተነስተው ቻይና ከመግባታቸው በፊት ለጢያራቸውም  ለተከታዮቻቸውም እህል ውሀ ለማለት ሳይሆን አይቀርም፤ የባንግላዴሽ ዋና ከተማ ከሚገኘው ‘ሀዝራት ሻሃጃላል ጢያራ ጣቢያ’ አረፍ ብለው ነበር። በማግሥቱ የቻይናው ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ኬቂያንግ ጥያራ ጣቢያ ተገኝተው ተቀበሏቸው። ዓርብ ደግሞ ከአዲሱ የቻይና ፕሬዚደንት ጋር ውይይት አደረጉ። ቅዳሜን እዚያው ውለው አድረው እሑድ ከአገር ወደተነሱበት ቁም ነገር ለመመለስ ወደሎንዶን ‘ስታንስተድ’ ጥይራ ጣቢያ አመሩ። የሎንዶኑ አቀባበል ከቤይጂንጉ የላቀ ይሁን የደበዘዘ የምናውቀው መረጃ የለንም።

Sunday 14 April 2013

“ተፈራ ደገፌ በቫንኩቨር ፀጉር ማስተካከያ ቤት የዘረኝነት መድሎ ተፈጸመብኝ አለ”


ኼንን ዘገባ ይዞ የቀረበው ጋዜጣ “የዕለቱ ዩቢሲ” (The Daily Ubyssey) የሚባለው የ’ብሪቲሽ ኮለምቢያ ዩኒቨርሲቲ’ ልሣን ሲሆን ታሪኩን ያዘለው ዕትም ለንባብ የቀረበው ዓርብ መስከረም ፲፭ ቀን /ም ነበር።  ልክ ነዎት አልተሳሳቱም! አሥራ ዘጠኝ መቶ አርባ ዓመተ ምሕረት፤ የዛሬ ስድሳ ስድስት ዓመት ማለት ነው!

Sunday 3 February 2013

አስፋ ወሰን ኃይለ ሥላሴ - ክፍል ፪


«እሳት በሌለበት ጭስ የለም!» ወይስ «ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ!» ?


ክፍል ላይ በልዑል አልጋ ወራሽ መርዕድ አዝማች አስፋ ወሰን ኃይለ ሥላሴ ስም ተጻፈ የተባለ፤ ሕሊናን የሚረብሹ ነጥቦችን ያዘለ ደብዳቤ ተመልክተናል። በታኅሣሥ ፶፫ቱም የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ያተረፉትን፤ እንደሙጫ ስማቸው ላይ ተጣብቆ የቀረውን ሐሜታም ተመልክተናል።

፪ኛው ክፍል ደግሞ የምንዳስሳቸው የብሪታኒያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብት ሰነዶች በተለያዩ ጊዜያት አልጋ ወራሹ ከብሪታኒያ ርዕሰ-ልዑካን እና ከአሜሪካው ርዕሰ-ልዑካን ጋር ያካሄዷቸውን ሰፊ ውይይቶችና በወቅቱ የአገር ፖለቲካ ላይ ለነኚሁ የባዕድ መንግሥታት ወኪሎች የሰጡትን አስተያየት ያካትታል።

Sunday 27 January 2013

አስፋ ወሰን ኃይለ ሥላሴ - ክፍል ፩


(ከድል እስከ ታኅሣሡ ጉሽ)

ቻርድ ግሪንፊልድ የልዑል አልጋ ወራሽ መርዕድ አዝማች አስፋ ወሰን ኃይለ ሥላሴን ሞት ተከትሎ በብሪታንያው ‘ኢንዲፔንደንት’ ጋዜጣ ላይ በጻፉት የሙት መወድስ (ኦቢችዋሪ) ላይ «መስከረም ፲፯ ቀን ፲፱፻፱ / መኳንንቱ እና  የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንቱ በተሰበሰቡበት አቡነ ማቴዎስ የልጅ ኢያሱን መሻር እና መወገዝ ሲያበስሩ፤ ሕፃኑ አስፋ ወሰን በአንቀልባ ታዝሎ ከሁለት አሽከሮች ጋር እንግሊዝ ለጋሲዮን ተደብቆ ነበር።»[1] ይላሉ።

Monday 21 January 2013

ወይዘሮ ዘውዲቱ፤ ራስ ጉግሳ ወሌ እና ቀብራራው አርምብራስተር!



ንደው እመ-ብርሃንን ወገኖቼ፤ የነጮች ጥጋብ ሁሌ እንደገረመኝ ነው!

እውነት ነው በአሥራ ዘጠነኛው እና በከፊልም ቢሆን በሀያኛው መቶ ክፍለ ዘመን፤ በተለይም እንግሊዞቹ እና ፈረንሳይቹ ጉልበተኛ ፈላጭ ቆራጭ ስለነበሩ የንቀታችውን መጠን ግፋ ቢል፤ በአዕምሮ ሚዛን ልንረዳላቸው እንችል ይሆናል። ያውም እኛ ኢትዮጵያውያን እራሳችንን ከሌሎቹ ገለል አድርገን የነጮቹን አስተሳሰብ የተገነዝብልናቸው እንደሆነ ነው።
ወደዋናው ጉዳይ ከመመለሴ በፊት አንድ የሰማሁትን ላካፍላችሁ።  በሃያኛው መቶ ክፍለ-ዘመን አገር ለመጎብኘት (መጎብኘት ሲባል መሰለል ብለው ያንብቡ!!!!) የገባ እንግሊዛዊ ወደአገሩ ለመመለስ በባቡር ከአዲስ አበባ ወደ ጂቡቲ እያመራ ነው።  እንግሊዛዊው እንደለመደው በአንደኛ ደረጃ ክፍል እያነጎደ ነው። የእኛ ሰዎች ግን በገዛ አገራቸው፤ የአንደኛ ደረጃውን ካርኔ ከአቅም በላይ እንዲሆን አድርገውባቸው ይሆናል፤ ብቻ ምን አደከማችሁ አንባብያን! በሦስተኛ ማዕርግ ላይ ነው ከመቶ ወደ ዘጠና ዘጠኝ ነጥብ ስድስት የሚያክሉት ተሣፋሪዎች የተጨቀጨቁት። (ነጥብ ስድስቱ ታዳጊ ወጣት መሆኑ ይሆን? ለነገሩ ግን ይሄ  ዘጠና ዘጠኝ ነጥብ ስድስት የሚሉ አመዛዘን ያኔም ነበር ማለት ነው? ወይስ አዲስነቱ ለሕዝብ ሸንጎ ቆጠራ ነው? )

Friday 13 May 2011

«ተጨናቂው የኢትዮጵያ አንበሳ»



በታኅሣሥ ወር ፲፱፻፶፫ ዓመተ ምሕረት የተከሰተው የነመንግሥቱ ነዋይ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የኢትዮጵያን ንጉዛት አናውጦት ካለፈ ዓመት ከሦስት ወር ሆኖታል። ጄኔራል መንግሥቱም በዚያው ምክንያት በስቅላት ከተገደሉ እነሆ ዓመት አለፋቸው። እቴጌ መነንም ከተለዩን ገና ሦስት ወራቸው ብቻ ነው። ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ብዙ የአፍሪቃ አገሮች ከአውሮፓውያን የቅኝ ግዛት ቀንበር ተላቀው የነፃነት እግራቸውን በዳዴ ለማጠናከር እየተፍጨረጨሩ ነው።

ታዲያ በዚያ ወቅት የአሜሪካው ‘ታይም’ መጽሔት ግንቦት ፳፬ ቀን ፲፱፻፶፬ ዓመተ ምሕረት፤ «ተጨናቂው የኢትዮጵያ አንበሳ» በሚል ርዕስ ያወጣው ዓምድ ስሜቴን በተለያየ መልክ የፈተነ ጽሑፍ ነው። መቸም መራራ ሐቅን እቅጭ አድርገው ሲነግሩት የሚያሽረው ጥቂት ነውና። 

በመግቢያው አንቀጽ ላይ የአዲስ አበባ ሴት ዝሙት አዳሪዎች ማስተወቂያቸው “ቀይ መስቀል” ነበረ። ነገር ግን የዓለም አቀፍ የቀይ መስቀል ማኅበር መዝናናት የሚፈልጉ ብዙ ወንዶች እየተሳሳቱ በየክሊኒኮቼ ዘው እያሉ አስቸገሩኝ በማለቱ፤ እነኚህ ሴቶች ምልክታቸውን ወደ ቀይ መብራት እንዲለውጡ የመንግሥት ድንጋጌ መውጣቱን ያበሥራል። ታዲያ ይሄ ድንጋጌ ሥራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ የነኚህ የወንድ መዝናኛ ቤቶች ከአምስት ሺ ወደ ስምንት ሺ ማደጉንና የአካባቢው የመብራት ኃይል ፍጆታም ማሸቀቡን ይዘግባል።

ዛሬ ቢሆን “የኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት በእጥፍ አኃዝ ማደጉን የ’ታይም’ ጋዜጠኛ መሰከረ።” ነበር ርዕሰ አንቀጹ የሚለው።

 ‘ታይም’ እድገቱ የወቅቱን ለውጥ እንደሚያረጋግጥ ሲጠቁም፤ ምክንያቱንም ኢትዮጵያን የአፍሪቃ ነጻነት ትግል እምብርት ለማድረግ ንጉሠ ነገሥቱ የሚያደርጉት ጥረት በርዕሰ ከተማዋ በሚካሄዱት ሥፍር-የለሽ ስብሰባዎች ላይ ለመሳተፍ የሚጎርፉት እንግዶች ናቸው ይላል።  [ሌላው ቢቀር፣ ሽርሙጥና ከፍ ያለ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ሆነልን ማለቱ ይሆን? የትም ፍጪው፣ ዱቄቱን አምጪው! ይባል የለ?]

ወደታሪክ መለስ ብሎም «እነኚህ ዘራቸውን ከንጉሥ ሰሎሞንና ከንግሥት ሣባ በመምጣቱ የሚኮሩ
ኢትዮጵያውያን - ለብዙ ምዕት ዓመታት ጥቁር አፍሪቃውያንን “ባሪያ” እያሉ በማንቋሸሽ ኖረዋል።» ነገር ግን የጥቁር አፍሪቃ አገራት ነፃ እየወጡ ድምጻቸውን በዓለም መድረክ ላይ ማሰማት ከጀመሩ በኋላ ንጉሠ ነገሥቱ፣ ድሮ “ባርያ” እየተባሉ የሚናቁትን አሁን ግን «ተወዳጅ ጥቁር ወንድሞቻችን» በሚል ለአኅጉሩ መሪዎችና ታጋዮች የቅኝ-ግዛትን ሥርዓት በማውገዝ በደብዳቤ መልዕክቶቻቸውን ማብረር ጀመሩ። ካለ በኋላ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሰሞኑን በ ሦስት ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ($3,000,000) በተገነባው አዲሱ የ’አፍሪቃ አዳራሽ’ ውስጥ ተንቀሳቃሹን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የቅኝ  ግዛት ሸንጎ አባላትን እንደሚያስተናግዱ ይነግረናል። ከካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው አንዱ “ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደዚህ አይነት መስተንግዶ ለአፍሪቃ አኅጉር መሪነት ያላቸውን ምኞት እንደሚያሳካላቸው ያምናሉ” ይላል ።

ይኸው ኢትዮጵያዊ የካቢኔ ሚኒስቴር «እኛ ከሁሉም የቆየ ነፃነት አለን። በቅርብ ነፃነታቸውን የተቀዳጁትን ወንድሞቻችንን ደግሞ ወደዘመናዊው ዓለም የመምራት ግዴታችንም ቅርሳችንም ነው» ብሏል በሚል ጽሑፉን ያዘጋጀው የመጽሔቱ ቃል አቀባይ ጠቅሶታል። ታዲያ የጽሑፉ ደራሲ ጋዜጠኛ «ይቺ ከዓለም ኋላ ቀር አገሮች መኻል የምትሰለፍ አገር፤ ፓርላማዋ ሥራውም ሆነ ችሎታው የንጉሠ ነገሥቱን ፍጹም ሥልጣን በማኅተም መርገጫ የማጽደቅ ብቻ የሆነባት እና የመገናኛ ብዙሐን ነፃነት የማይከበርባት፤ ሰላዮችና ጆሮ ጠቢዎች በሰፊው የተሠማሩባት ኢትዮጵያ እንኳን ሌላ አገሮችን ወደዘመናዊው ዓለም ለመምራት ቀርቶ፣ እራሷም መንገዱ በየት እንደሆነ አይታውም አታውቅ።» በሚል ከእሳት ማዕበል የበለጠ በሚፋጁ ቃላቶቹ ሸንቁጦናል። የምታቦካው የላት የምትጋግረው አማራት አሉ አባቶቻችን!
ይሄ ብቻ መቼ በቃውና! ያ ብስለት የጎደለው፣ ጉረኛ [እንዲያውም ትዕቢት የተሞላበት ቃላቶች በመሰንዘሩም ‘አሳዳጊ የበደለው ባለጌ’] የካቢኔ ሚኒስቴር በሰነዘራቸው ቃላት መነሻነት ለጋዜጠኛው የስድብ ነጎድጓድ ዳርጎናል። ሞኝና ወረቀት የያዙትን አይለቁም እንደሚባለው ከልጅነቱ ጀምሮ ሲሰማው የቆየውን የስህተት አመለካከት ማረም እንኳ ያልቻለ ትሩማንትሪ!
መቸም በዚህ ጽሑፍ ላይ የሠፈሩትን ነጥቦች እውነተኛነት ላለመቀበል ሳይሆን፤ በባእድ ብዕር መሰደባችን እየከነከነኝ ነው። «ወንጀለኛ በአደባባይ የሚሰቀልበት አገር፣ ከነአካቴው የወህኒ ቤቶችን መጣበብ ለማቃለል እና ለ’እኔን አይተህ ተቀጣ’ም እንዲያመች በእሥራት ፋንታ በአደባባይ መገረፍ በቅርቡ ተፈቅዷል » ይልና፤ ስለሙስናም ሳይተርብ አያልፍም። በዘገባው እንዳሰፈረው ባለ ሥልጣናቱ በሙስና ከመጨማለቃቸው ብዛት ከሚሰበሰበው ቀረጥ ሲሦው ወደመንግሥት ካዝና አይገባም ብሏል።

የመንግሥቱ የአስተዳደር ብዛትና ክብደት ከአገሪቱ ዓመታዊ ወጭ ሁለት ሲሦውን ይበላዋል፤  በሀያ ሚሊዮን የሚገመተው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከአገሪቱ ሀብት የሚደርሰው በዓመት በአማካይ አምሥት የአሜሪካ ዶላር እንደሆነ፤ ከመቶ ሕዝብ ዘጠናው መሐይም፤ ሰማንያ በመቶው ደግሞ በጥገኛ ነፍሳት የተጠቃ፤ ገሚሱ የወሲብ በሽታ የተጸናወተው እና አርባ ከምቶ የሚሆኑ ሕጻናት እንደሚሞቱ፤ ወባ በየዓመቱ ሰላሳ ሺ ሰዎችን እንደሚገልና ከመቶ ከብቶች አርባዎቹ በሳምባ ነቀርሳ የተለከፉ እንደሆኑ ይተነትናል።

ኧረ በፈጠረህ ይበቃል! አልኩኝ ፣ አጠገቤ ያለ መስሎኝ!
እሱም «አንዴ ጀምሬዋለሁና በትእግሥት አስጨርሰኝ» የሚለኝ መሰለኝ። ለጥቆም «የነጮች ልምዳዊ ማሳጣት ነው፤ ይሄን ሁሉ የሚያስተነትንህ እያልከኝ አይደል? እሺ የኔንስ እንደዚያ ገምተው። ስብሰባ ላይ ሊሳተፍ የመጣውስ ጥቁር፤ አፍሪቃዊ፤ ሴኔጋላዊስ? ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?» ይለኛል። አያችሁ በታሪክ አውሎ ነፋስ እይተውዠገዠገ መጥቶ ልቦናዬን እንዴት እንደሚያስተኝ? ወቸ ጉድ!

ይሄ ሴኔጋላዊ የአዲስ አበባን አራት መቶ ሃምሣ ሺ ነዋሪዎች ድህነት፤ መራቆት እና  የኋላ ቀር ኑሮ ከተገነዘበ በኋላ “የነፃነት ውጤት ይሄ ከሆነ፤ መልሳችሁ ግዙኝ።” ብሎኛል አለ ጸሐፊው። ያ ምስኪን ሴኔጋላዊ ነፃነትን በቀመሰ በሁለት ዓመቱ እንኳንስ እኛን እንደመሪ ሊቆጥር ጭርሹንም የእኛ ኑሮ አቅለሽልሾት ነፃነቴ ይቅርብኝ እስከማለት መድረሱ ለጋዜጠኛው አመለካከት ድጋፍ እንደሰጠውና የዚያም የካቢኔ ሚኒስትር አጉል ድንፋታ ፍሬ-ቢስ እና ውዳሴ ከንቱ መሆኑን በማያሻማ መልክ አረጋግጦታል። ጉድ እኮ ነው!

ተንኮለኛው ዘጋቢማ ምን ዕዳ አለበት? «ይሄ ሁሉ [ኋላ ቀርነት] ለጞብኚ አፍሪቃውያን ምን ዓይነት አሉታዊ ስሜት እንደሚፈጥር የተገነዘቡት ንጉሠ ነገሥት»፣ ይላል አሜሪካዊው፤ «የኢንዱስትሪያዊ ልማት ከመጀመራቸውም ባሻገር ግድቦችን፤ ነዳጅ ማጣሪያ፤ ወደቦችን እና ፋብሪካዎችን ለማሠራት ከምዕራባውያንም ከምሥራቃውያንም ዕርዳታ እየተቀበሉ ነው።» ዳሩ ግን የራሳቸውን ሥልጣን ይቀንሱብኛል ብለው የሚያምኗቸውን የአስተዳደር እና የፓርላማ ማሻሻያ እርምጃዎችን ለመውሰድ አሻፈረኝ እንዳሉም አብሮ አስፍሯል። ከአሥራ ሰባት ወራት በፊት በንጉዛቱ ሥርዓት ላይ ተነስተው የነበሩት ምሑራን እና ተራማጅ ወገኖች፤ ምንም እንኳ የኃይለ ሥላሴ መንግሥት በሹመት፣ በሽልማት ሊደልላቸው ቢሞክርም እንቅስቃሴያቸው አልበረደም። ሆኖም እራሳቸውን በቅጡ ያላደራጁ እና ቀጣዩ የተቃውሞ እርምጃ ምን መሆን እንዳለበት ስላልተስማሙ ጩኸትና ጫጫታቸው አልተተገበረም።

የትንተናውን ድምዳሜ በንጉሠ ነገሥቱ ላይ በማተኮር፤ «የ፷፱ ዓመቱ ሽማግሌ በባለቤታቸው እና አራት ልጆቻቸው ሞት ብቸኛ ቢሆኑም እንኳ ከሃያ ስድስት ዓመታት በፊት በዓለም መንግሥታት ማኅበር መድረክ ላይ በመቆም ያሳዩት የጉልምስና ስሜት አሁንም አልራቃቸውም።» የ፵፭ ዓመት ዕድሜያቸውን የያዙት ልጃቸው አልጋ ወራሽ አስፋ ወሰን ግን ከአባትዬው ይልቅ የተራማጅነት አስተሳሰብ ያላቸው ቢሆኑም ባህሪያቸው ለስላሳ እና ጨፍጋጋ ነው ይልና፣ «የንጉሠ ነገሥቱ ዘውድ ሳይተላለፍ ብዙ የዘገየ እንደሆነ፤ በአሮጌው ሥርዓት ላይ ያለመው መሣሪያ ምላጭ መሳቡ የማይቀር ነው።» ሲል ዘገባውን ደምድሟል። ምከረው ምከረው እንቢ ካለ መከራ ይምከረው እንዲሉ፤ ጃንሆይም አልሰማ ብለው….

በሚቀጥለው የታሪክ አውሎ ነፋስ እስከምንገናኝ፤ የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ!


Thursday 28 April 2011

የየዋሖቹ ዘመን

አንድ ሻምበል ሄንሪ ዳርሊ የሚባል፣ አገር እቀኛለሁ፣ አረመኔ አሰለጥናለሁ ባይ እንግሊዛዊ በ 1899 ዓመተ ምሕረት ከአሁኗ ኡጋንዳ ተነስቶ በደቡብ-ምዕራብ ኢትዮጵያ በኩል ወደ ዳግማዊ ምኒልክ ተልኮ ሲጓዝ፤ በመንገድ ገጠሙኝ ከሚላቸው ሁኔታዎች አንዱ ከዚህ የሚከተለው በ'ባሪያዎችና የዝሆን ጥርስ' (Slaves & Ivory)ብሎ በሠየመው መጽሐፉ ላይ ያሰፈረው አስቂኝ ነው።


ከ ጅማ የተነሳን ዕለት ከበቅሎዎቼ ሁለቱ አምልጠው የሰው ጤፍ ማሳ ውስጥ ይገቡና እሽቱን በልተው ሲጠግቡ [የተፈጥሮ ግዴታቸው ነውና] ሌላውን እየንተንከባለሉ የዚያን የምስኪን ገበሬ ምርት አጥፍተውበት ኖሯል። እኔ ደግሞ ከማረፊያ ግቢዬ መጥፋታቸውን ስገነዘብ ፈላጊዎች ልኬ፣ ሰዎቼ ወዲያው በቅሎዎቹን እየነዱብቅ ሲሉ አብረዋቸው ብዙ ኦሮሞዎች እየተጯጯሁ በግርግር ተከትለዋቸው እግቢዬ ገቡ። ታዲያ የጤፉ ባለቤት የበቅሎዎቹ ጌታ እኔ መሆኔን ሲገነዘብ፣ ሸማውን አጣፍቶ ተጠጋኝና እሱ በቁጣ መሰል ጩኸት፣ አጃቢዎቹ ደግሞ አየር ለመሳብ ባረፈ ቁጥር በጭብጨባና ሆሆታ ብዙ ደነፉብኝ። እኔ ግን ኦሮምኛ ባለማወቄ ምን ጉድ እንደተፈጠረ ሊገባኝ አልቻለም። ደግነቱ ከተከታዮቼ አንዱ በስንት መከራ ድምጹን ለማሰማት ችሎ ሰውዬው ችግሩ ምን እንደሆነ ገለጸልኝ።

ለካስ እንዲህ ያቁነጠነጠውና ደም-ሥሩ እስኪገተር ያስደነፋው የኔ በቅሎዎች ማሳውን ያጠፉበትን ኪሣራ እንድከፍለው ኖሯል። እኔም ወዲያው ገንዘብ ያዢዬን ጠራሁና አንድ ብር ባሰጠው፣ ብሩን እያገላበጠ አፉ እስኪደርቅ ድረስ በዚያው ኦሮምኛው ይለፈልፍ ጀመር። 'ለጉዳቴ በቂ አይደለም' የሚለኝ መሰለኝና አንድ ብር አስጨመርኩለት። እንዲያውም ባሰበት! እኔም ጩኸቱ ሰለቸኝና 'በቃ ሁለት ብር ጨምርለት አልኩ፡' አራት ብር
አይበቃኝም ካለ ወደዳኛ ሄዶ ይክሰሰኝ በሉት አልኩና ደመደምኩ።

ገበሬው አራት ብሩን በጁ ይዞ፣ ተስፋ በቆረጡ ዓይኖቹ ካተኮረብኝ በኋላ ጩኸቱን አቁሞ በቅሎዎቼ ካታሰሩበት ፈታና እየነዳ ከግቢዬ ወጥቶ ሰደድ ብሎ እዚያው ማሳው ወስዶ ለቀቃቸው። የኔ ሰዎች ታዲያ በጉልበት ቀምቶ መውሰዱ ነው ብለው ሊያስጥሉት አካኪ ዘራፍ ብለው ነበር። ተዉት! እንደዚህ በዚህ ሁሉ ሰው ፊት ሊሰርቃቸው አይችልም። እስቲ እልሑ ይውጣለት ብዬ አረጋጋኋቸው እንጅ።

በኋላ ሲያስረዱኝ ለካስ ሰውዬው ካሣ ብሎ የገመተው (የጠበቀውም) አምሣ ሣንቲም የማያወጣ ሁለት አሞሌ ጨው
ኖሯል። አንድ ብር ሲሰጠው እንደዚያ ያጉረመረመው ለካ 'ለዚህ ምንዛሪ አሁን ከየት እንዳመጣልህ ነው?' እያለ ኖሯል። ሁለት ብር ሲሆንለት ደግሞ የባሰውን 'ምን አይነት ደንቆሮ ሰው ነህ? ብሎ እየተገረመ ኖሯል። ይሔም አልበቃ ብሎ አራት ብር ሲሆን በቅሎዎቹን መልሶ ማሳው ውስጥ የከተታቸው ለካ፣ 'በል እንግዲህ ከማሳው እህል ዋጋ እጅግ በላይ አድርገህ ከፍለሃልና ሒሣብህ አይቅርብህ! በቅሎዎችህም የቀረውን እንደልባቸው ይብሉትም ይንከባለሉበትም" ማለት ኖሯል።
እንግዲህ ያ ዘመን በአገራችን የሚመረጠው መገበያያው የማርያ ጠሬዛ (ጠገራ) ብር እና አሞሌ ጨው የነበረበት ዘመን፤ [ዳግማዊ ምኒልክ ከዚህ አጋጥሚኝ 13 ዓመት በፊት አንድ ብር፣ የብር ግማሽ፣ የብር ዕሩብ፣ የብር ስምንተኛ እና የብር ሃያኛ ዋጋ የነበራቸውን ሣንቲሞች አሰራጭተው ቢሆንም እንኳ!] አባቶቻችን ሐቅን ተመርኩዘው መብታቸውን ከማስከበር ወደኋላ የማይሉበት፤ በሐቅ በወዛቸው ያላፈሩትን የማንንም ንብረት የማይመኙበት ዘመን መሆኑን ልብ ይሏል።

ይህ ክስተት ዛሬስ ቢሆን ኖሮ? ምን ዓይነት ዝገባ ይጻፍ ይሆን?
የዚህን ተጓዥ አጋጥሚኝ ሳነበው የሳቅኹትን ያህል ያስገርመኝ ይሆን?
ያ የጤፍ ማሳ በትንሹ ተገምቶ አራት አምሥት ኩንታል እህል ያመርታል ብንል፣ አንዱ ኩንታል ከሺ ብር በላይ በሚያወጣበት በዚህ ከይሲ ዘመናችን፣ ያ ምስኪን ሐቀኛ የኢትዮጵያ ገበሬ ከሞት ዕንቅልፉ ቢነቃ ምን ይል ይሆን?

መልሱን ለየአንዳንዳችን ልቦና እተወዋለሁ።

በሌላ የታሪክ አውሎ ነፋስ ጽሑፍ እስከምንገናኝ ድረስ የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ።