Showing posts with label Ethiopia. Show all posts
Showing posts with label Ethiopia. Show all posts

Sunday 9 December 2012

የመቅደላው ዮሐንስ እሸቴ በሎንዶን



መቶ አርባ-አምስት ዓመት ያስቆጠረው መቅደላን ስናነሳ መቼም ዓፄ ቴዎድሮስና ታላቁ ጀብዷቸው፤ ሮበርት ናፒዬር እና እንግሊዞች በሀገራችን ላይ ያካሄዱት ከ‘ግዳጅ ወሲብ’ ጋር የማይተናነስ ደፈራ እና ብዝበዛ፣ የነደጃች ካሣ ምርጫ ሴራ፤ የልጅ ዓለማየሁ መሰደድና በለጋ ዕድሜው ከሀገርና ከዘመድ ተለይቶ ሳለ የሕይወቱ በአጭሩ መቀጠፍ፣ ወ.ዘ.ተ. ይታወሱናል። ስለዚያ ወቅት ታሪክ በጥልቀት ለሚያጠና፣ አያሌ መጻሕፍትና ማስታወቻዎች፤ አብዛኞቹ በነጮቹ፣ አንዳንድም በኛው ሰዎች ተጽፈው በታሪክ ማኅደር ውስጥ ይገኛሉ።

ታዲያ እነዚህን መጻሕፍት ስንመረምር፣ ከዋነኞቹ ተዋንያን ውጭ አልፎ አልፎ በጨረፍታ፤- መጠሪያ ስም ያልተሰጣቸው አያሌ ኢትዮጵያውያን ሲኖሩ አንዳንዴ ደግሞ ከታሪክ መዛግብት መኻል አንዳንድ የአበሻ ስሞች ገጹ ላይ ብልጭ ሲሉ እናያቸዋለን። በምንም መልኩ ቢሆን እነዚህን አበሾች ያንሷቸው፤ ለታሪክ ተማሪው/ተመራማሪው፤ በስደት ዓይናችን ለምናጤናቸው ግን ማን ነበሩ? በአገሪቱ ታሪክ ላይ የነበራቸው እውነተኛ ሚና ምን ነበር? መጨረሻቸውስ ምን ሆኖ ይሆን? የሚሉትን ጥያቄዎች ስለሚጭሩ ለግል እርካታና ጠለቅ ላለ ግንዛቤ መዳበር የሚረዳ ቅኝት ነው። አርኪ መልስ ግን እንደ ማስረጃዎቹ እጥረት የህልም ሩጫ ነው።

መቸም የነጮቹ ግምገማ አልፎ አልፎ በጥሩ መልክ ቢሆንም አብዛኛውን ጊዜ ግን በዚያው በዘረኝነት በተበከለው ብዕራቸው ሲለቀልቋቸውና ቀጣፊ፡ አታላይ፡ ዋሾ፡ ዘራፊ፡ ከሀዲ፡ አድርባይና ቀላማጅ ከሚሉ ቅጽላት ጋር እያጣመሩ እንደ ዐረመኔ ገልቱ ሲገልጿቸው ቢሆንም በኢትዮጵያዊ አመለካከታችን ከውስጡ ፈልቅቀን ለማውጣት የምንችለውን ቁም ነገር ግን ሊሸፍኑት አልቻሉም።

በዚህ መልክ ከምንተዋወቃቸው ኢትዮጵያውያን መሐል በከፊሉ፦
ሰናፌ የተወለዱት የደንቀሌው ባላባት ልጅ፣ በአረብኛ ቋንቋ የተካኑት እና ሚሲዮናውያኖቹ ካይሮ ወስደው ክርስትና ያነሷቸው ሳሙኤል ጊዮርጊስ፤ ከንጉሥ ሣህለ ሥላሴ፤ ከዓፄ ቴዎድሮስ እና ከዓፄ ዮሐንስ ጋር ታሪካቸው ተሰባጥሮ የሚገኝ ሲሆን በተለይም በመቅደላ ክስተት በባልደረባነት፤ በአስተርጓሚነት፤ በተላላኪነት፤ ወዘተ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል።

ሁለተኛው፤ በልጅነታቸው ዘመን አገር ለመዳሰስ የመጣው ሄንሪ ለፌቭር የተሰኘው ፈረንሳዊ ይዟቸው ወደአገሩ ከወሰዳቸው በኋላ እዚያው ሲማሩ በነበሩበት ወቅት ከፈረንሲሱ ንጉሥ ሉዊ ፊሊፕ ጋር መልካም ግንኙነት መሥርተው የነበሩ፤ በኋላም ወደእንግሊዝ አገር ተጉዘው ትምህርታቸውን ሲያዳብሩ ቆይተው በካይሮ በኩል ወደአገራቸው የተመለሱት የአድዋው ተወላጅ ዐለቃ  ማኅደረቃል ናቸው። ዐለቃ ማኅደረቃል በጠቅላላው ለ፲፩ ዓመታት በውጭ የቆዩ ሲሆኑ፣ የዓፄ ቴዎድሮስ አስተርጓሚ ሆነው ያገለግሉ እንደነበር ተዘግቧል።

ሌላው ደግሞ በልጅነት ዕድሜያቸው ከወንድማቸው ጋር በሚሲዮናውያኑ ወደ ሕንድ ተወስደው፣ እዚያው ተምረው ሲመለሱ መጀመሪያ በየደጃች በዝብዝ ካሣ ጸሐፊና አስተርጓሚ የነበሩት፣ በኋላም ጌታቸው ዓፄ ዮሐንስ ከተባሉ በኋላ ደግሞ ነጮቹ “ጠቅላይ ሚኒስትር” የሚሏቸው ፤ ወደ እንግሊዝ አገርና ንግሥት ቪክቶሪያ “ልዩ መላክተኛ” ተደርገው የተላኩት፣ እንግሊዝኛ ተናጋሪው ምርጫ ወርቄ ናቸው። እኒህ ሰው እንግሊዞች ወደመቅደላ ሲያልፉ መስፍናቸውን ወክለው ከጦር ዓለቆቹ ጋር በመደራደር የትግራይ ሕዝብና ሹማምንት በግብረ አበርነት መንፈስ እንዲተባበራቸው ያደረጉና በኋላም ሮበርት ናፒዬርና ደጃች ካሣ ማክሰኞ የካቲት ፲፰ ቀን ፲፰፻፷ ዓ/ም ግንባር ለግንባር ተገናኝተው ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ያደረጉ ናቸው።

ሌሎች ደግሞ በጦርነቱ ምክንያት እንደ ልዑል ዓለማየሁ ቴዎድሮስ፣ ወላጅ አልባ የሆኑ ወይም እዚያው ምሽጉ ውስጥ ተጠግተው የተገኙ ወይም ደግሞ ነጭ እስረኞቹን ተጠግተው ያገለግሉ የነበሩ፤ ጦርነቱ ሲገባደድም ነጮቹን ተከትለው የተሰደዱ ሕፃናት ነበሩ። አዛዥ/ሐኪም  ወርቅነህ  እሸቴ በዚህ ጊዜ የሦስት ወይም የአራት ዓመት ልጅ ነበሩ። ከጦሩ መልስ ወደ ሕንድ አገር ተወስደው እዚያው ያደጉ፤ የኖሩ እና በቀዶ ጥገና ሙያ የተሠማሩ ሰው ሲሆኑ አሳዳጊ አባቶቻቸው በሰጧቸው ስሞች ቻርልስ (በወሰዳቸው መኮንን ስም) ማርቲን (ባሳዳጊያቸው ሐኪም ስም) (Charles Martin) ይባሉ ነበር። አዛዥ ወርቅነህ ለመጀመሪያ ጊዜ በዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ዘመን ወደኢትዮጵያ ተመልሰው እንደነበርና ንጉሠ ነገሥቱም በታመሙ ወቅት ከሚያክሟቸው የጤና ባለሙያ አንድ እንደነበሩ ታሪክ ይዘግባል። በኋላም በሎንዶን የኢትዮጵያ ዋና መላክተኛነቱን ሥልጣን ተሹመው የፋሽስት ኢጣልያ መንግሥት የኢትዮጵያን ግዛት በሥሩ ማስተዳደር እስከጀመረ ድረስ ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

እንግዲህ እነዚህ በታሪክ አውሎ ነፋስ እየከነፉ በሕሊና ልቦናችን የምንቃኛቸው ኢትዮጵያውያን በሙሉ የየግል ታሪካቸው ትንተና እንደሚያስፈልገው አንዳችም ጥርጣሬ ባይኖርም፤ የዛሬው እንግዳዬ የመቅደላ ጦርነት ሲያከትም የአሥራ አራት ወይም የአሥራ አምስት ዓመት ወጣት የነበረው ዮሐንስ እሽቴ ነው። ይኼንን ኢትዮጵያዊ የምንተዋወቀውም ድምጹም የሚጠፋብን በንግሥት ቪክቶሪያ ዘመን፤ በአንድ መጽሐፍ ላይ ብቻ፤ በብሪታንያ ርዕሰ ከተማ ምዕራባዊ ጎን፣ ስቴይንስ(Staines) እና ሪችሞንድ (Richmond) ከሚባሉ መንደሮች ነው፤ እንዲሁም በኮቬንት ጋርደን እና በዋይት ሆሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቢሮ ነው።  

ዮሐንስ የዬት አገር ተወላጅ እንደነበረ ባናውቅም፤ ሰኔ ፳፬ ቀን ፲፰፻፶፪ ዓ/ም በንግሥት ቪክቶሪያ ተሹሞ ወደ ዓፄ ቴዎድሮስ የብሪታኒያ ሁለተኛ ቆንስላ ተብሎ[1] ወደአገራችን የተላከውና በአንዳንድ ምሑራን አስተያየት ለጦርነቱ መነሻ ክብሪት ነበር የሚባለውን ቻርልስ ዳንከን ካሜሮን (Charles Duncan Cameron, Esq.,)  መቅደላ ላይ ተጠግቶ ያገለግለው እንደነበርና ከእንግሊዞችም ድል በኋላ ይሄንኑ ካሜሮንን ተከትሎ በግብጥ በኩል አድርጎ ወደ እንግሊዝ አገር እንደገባ ተራኪው አስፍሮታል። ካሜሮን ከመቅደላ እስራት ሚያዝያ ፬ ቀን ፲፰፻፷ ዓ/ም ተፈቶ ወደብሪታኒያ የተመለሰው በሐምሌ ወር ፲፰፻፷ ዓ/ም እንደነበር እና በስድስት ወሩ ጡረታውን አስከብሮ ኑሮውን ዠኔቭ ላይ መሥርቶ ሲኖር እዚያው በስዊሷ ከተማ ግንቦት ፳፫ ቀን ፲፰፻፷፪ ዓ/ም እንደሞተ ከሌላ የታሪክ መዝገብ እንረዳለን። ታዲያ ዮሐንስ ጌታውን ተከትሎ ወደዠኔቭ ተጉዞ ይሆን? ከሆነስ ካሜሮን ሲሞት እሱ እንዴት ሆነ? እንቀጥልና የሰር ኤድዋርድ ትረካ ስለዚህ ምዕራፍ ምን እንደሚል እንየው።

የዮሐንስ እሸቴን (በደራሲው አጻጻፍ፣ JOHANNES SCHATEY) እጅግ አጭር ታሪክ የሚዘግበው፤ በወቅቱ በብሪታኒያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይሠራ የነበረውና “በዚያ ወቅት የቆንስል ካሜሮን የግል ወኪል” ነበርኩ የሚለን፤ ለብዙ ዓመታት የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፣ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኃላፊ የነበረው ሰር ኤድዋርድ ኸርትስሌት (SIR EDWARD HERTSLET, K.C.B.) ነው። ይኼም ዘገባ እ.አ.አ በሺ ዘጠኝ መቶ አንድ (፲፰፻፺፫ ዓ/ም) በታተተመው “የቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ትውስታዎቼ” (RECOLLECTIONS OF THE OLD FOREIGN OFFICE) በተባለ መጽሐፉ ላይ ይገኛል።

ሰር ኤድዋርድ ዮሐንስ እሸቴን የሚያስተዋውቀን፤ “ሰር ሮበርት ናፒዬር የብሪታኒያን ሠራዊት እየመሩ መቅደላ ምሽግ ሲደርሱ ወደ ንጉሠ ነገሥት ቴዎድሮስ እስረኞቹን በፈቃዳቸው ካልፈቱ መቅደላን በኃይል እንደሚደመስሱትና እስረኛ ወገኖቻቸውን ነፃ እንደሚያወጧቸው መላክ የፈለጉትን ደብዳቤ ‘ማን ያድረስ?’ የሚለው ጥያቄ ተነስቶ እንደነበር መስማቴን አስታውሳለሁ።” በሚል ሐረግ ሲሆን፤ ቀጥሎም “ከእስር በፊትም በእስር ጊዜም የካፕቴን ካሜሮን አገልጋይ የነበረው፣ በግምት የአሥራ አራት ዓመቱ ወጣት፣ ሎጋ፣ መልከ-መልካሙ ዮሐንስ እሸቴ በራሱ ፈቃደኛነት ‘እኔ አደርሰዋለሁ’ ብሎ፤ ለራሱ ደህንነት ምንም ሳያስብ፣ ደብዳቤውን አደረሰ” ይለናል። ሰር ሮበርት ናፒዬርም ለዚህ ጀብዱው ፳፭ ይሁን ወይም ፶ የእንግሊዝ ፓውንድ እንደሸለሙት ተነግሮኛል ይልና በኋላ ይህ ኢትዮጵያዊ ወጣት ካሜሮንን ተከትሎ ወደብሪታኒያ ለመጓዝ ሲነሳ ግማሹን ገንዘብ ለ’ወላጆቹ’ ሰጥቶ ግማሹን ይዞ ተጓዘ ይላል፣ ሰር ኤድዋርድ።

በወቅቱ መቅደላ ልይ ታስረው ከነበሩት ነጮች አንዱ፤ ሐኪም ሄንሪ ብላንክ ደግሞ፣ ሐምሌ ፲፯ ቀን ፲፰፻፷ ዓ/ም በታተመው “በአበሻ ምድር የእስረኝነት ትንታኔ” (A Narrative of Captivity in Abyssinia) በተሰኘው መጽሐፉ ላይ፤ ሰር ሮበርት ናፒዬር ስለላከው ደብዳቤ ሲተርክ፣ “ከጥቂት ቀናት በፊት የጦሩ ጠቅላይ አዛዥ ወደንጉሠ ነገሥቱ ደብዳቤ እንዲልኩ” ጄኔራል ሜሪዌዘር እንዲያስታውሷቸው ብዬ የላኩት ወጣት ልጅ ዛሬ [ሚያዝያ ፫ ቀን ፲፰፻፷ ዓ/ም] ከክቡር ጠቅላይ ጦር አዛዡ ለንጉሠ ነገሥቱ የተጻፈ ደብዳቤ ይዞ ሰፈራችን ደረሰ” ብሏል። ይሄንን መላክተኛ እገሌ ብሎ ባይጠራውም የሁለቱን ደራስያን ዘገባዎች ማዛመድ የሚቻል ይመስለኛል።

ሰር ኤድዋርድ የዮሐንስ ‘ወላጆች’ እነማን እንደነበሩ ወይም ዮሐንስና ካሜሮን እንዴት? በየት? ከማን ጋር? መቼ? ከኢትዮጵያ ተነስተው ግብጽ እንደደርሱ አይነገረንም። የሰር ኤድዋርድ ዘገባ ግን በቀጥታ ግብጽ ምድር ያገባንና ከዚያም ወደ እንግሊዝ አገር ለመነሳት ሲዘጋጁ ካፕቴን ካሜሮን ዮሐንስን ‘በጣም አሸብራቂ’ ልብስ - ሰማያዊ የግብጽ እጀ-ጠባብ ሱሪ፣ በብር አዝራሮች ያሸበረቀ ሰደሪያ፣ አረንጓዴ እጀ-ሰፊ የግሪክ ኮት እና ቀይ የቱርክ ‘ፌዝ’ (ኮፊያ) አልብሶት ነበር ይለናል። ሎንዶንም እንደደረሱ የዮሐንስ አሸብራቂ ልብስና የበለጠውንም እጅግ ብሩሕ ፈገግታው ብዙ ትኩረት እንደሳበና የካፕቴን ካሜሮን ወዳጆች በየተገኙበት ቦታ በተለይም በሴቶቹ በኩል የላቀ ተፈላጊነትና እውቅና ሰጥቶት እንደነበር ያወሳል።

በዚያ ወቅት፤ ከአንድ ስፍራ ላይ ሁለት በእድሜም ሆነ በሚጠብቃቸው የሕይወት ዕጣ ፈንታ የተለያዩ ኢትዮጵያውያን፤ በተለያዩ እንግሊዛውያን ከአገራቸው ተወስደው እንደነበር ልብ ይሏል። አንዱ ወደሕንድ ሲወሰድ ሌላኛው ደግሞ እንግሊዝ አገር ላይ የምናገኛቸው አዛዥ ወርቅነህ እሸቴ እና ዮሐንስ እሸቴ ሲሆኑ፤ ከስም አልፈው ታላቅና ታናሽ ወንድም ሊሆኑ ይችሉ ይሆን? ሁለቱም በጊዜው መቅደላ ላይ ታስረው የነበሩት የነጋድራስ እሸቴ ወልደማርያም ልጆች ይሆኑ?

በሎንዶን “ከዕለታት አንድ ቀን፣” ይላል ሰር ኤድዋርድ “ዮሐንስ ካሜሮንን ተክትሎ በሰረገላ ‘ሪጀንት ስትሪት’(Regent Street) በተባለው ጎዳና ካሉ መደብሮች ውስጥ ከተገበያዩ በኋላ ሲወጡ ከመደብሩ አሻሻጭ ልጃገረዶች አንዷ ለዮሐንስ በስጦታ ፊሽካ አበረከትለች” ይለንና “ብርቅዬ የሆነበት ዮሐንስ ሰረገላው ላይ ሆኖ ፊሽካውን ያቀልጠው ጀመር” ታዲያ አላፊ አግዳሚው የ ሎንዶን ሰው የፊሽካው ጩኸት ትርጉሙ ስላልገባው ግራ ተጋብቶ እንደነበር ዘግቦታል።

ዮሐንስ በእንግሊዝኛ ቋንቋ መግባባት ቢችልም በንባብ ዕውቀቱን ለማዳበር የነበረውን ጥረት ሰር ኤድዋርድ ሲያስረዳን “ካፕቴን ካሜሮንን እየተከተለ እኔም ቤት ይመጣ ነበር፤” ይልና “ከኪሱ የመሠረተ ንባብ ደብተሩን ያወጣና የማያውቃቸውን ሰዎች እንኳ ‘ማንበብ አስተምሩኝ’ይል ነበር” በሚል መልክ መጽሐፉ ላይ አስፍሮታል። ለጥቆም “ወጥ-ቤቷም ‘ኤሊዛም’ (ከቤት ሠራተኞቹ አንዷ መሆኗ ነው) ሁሉም የቤት ሠራተኞች ማንበብ ይችላሉ፤ እኔንም አስተምሩኝ” እያለ ዮሐንስ ይማለድ እንደነበር ይነግረንና “ታዲያ ከማንም ሰው ብዙ እርዳታ ያገኘ አይመስለኝም።” በማለት ይደመድማል።

ካፕቴን ካሜሮን እያስከተለው ወደውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያመጣው እንደነበረና ወደቆንስላው ኃላፊ ቢሮ ሲሄድ ዮሐንስን ሰር ኤድውራድ ቢሮ ትቶት በሚሄድበት ጊዜ “ዮሐንስ እኔ ምንጣፍ ላይ ይዘረጋ ነበር” ታዲያ ከዕለታት አንድ ቀን “ወደቢሮዬ ስመለስ ዮሐንስ ምንጣፌ ላይ እንደተጋደመ እሳት ሲሞቅ እንቅልፍ ጭልጥ አድርጎት አገኘሁት።” ይላል

በዚህ ወቅት፣ እንደ ሰር ኤድዋርድ ዘገባ፤ ካፕቴን ካሜሮን ስቴይንስ (Staines) በሚባለው አጥቢያ ካፕቴን ዲ ብቻ በሚለው ከእህቱ ባል ጋር ተዳብሎ ይኖር እንደነበር ይነግረንና ካሜሮን ግን ከተማው ውስጥ ሆቴል ማደር ያዘወትር ነበር ይለናል። ዮሐንስ ታዲያ ካፕቴን ዲ ወሮ በላ ይዘርፈዋል ከሚል ሥጋት በመነሳት እንዳይወጣ ቢከለክለውም እንኳ አካባቢውን ለብቻው እየዞረ ይውል እንደነበር፤ ያለችውንም ገንዘቡን ሁሌ በኪሱ እየያዘም ይወጣ ነበር ካለን በኋላ አንድ ቀን ካፕቴን ዲ በጣም ተቆጥቶት እምቢ ያለ እንደሆን በሰንሰለት እንደሚያስረው ዛተበት ብሏል። ጌታው ካፕቴን ካሜሮን መቅደላ ውስጥ ለዘጠኝ ወራት እግሩን ከጁ ጋር በሰንሰለት ታስሮ እንደነበር የቅርብ ትውስታው የነበረው ዮሐንስ ታዲያ ‘በሰንሰለት ትታሰራለህ’ ሲባል እድል እስኪያገኝ አድፍጦ ከቆየ በኋላ ከስቴይንስ ጠፍቶ ወደአሥር ማይል ያህል በግሩ ተጉዞ ሪችሞንድ (Richmond) ወደነበረው የሰር ኤድዋርድ ቤት ድረስ ኮብልሎ ገባ።

ሰር ኤድዋርድ ስለዚህ ጉዳይ ሲያወሳ “አንድ ቀን ከሥራዬ ስገባ ዮሐንስን በጣም ተከፍቶና የካፕቴን ዲን ቤት ጥሎ በመምጣቱ ምን ዓይነት ቅጣት ይደርስብኝ ይሆን በሚል ተጨናንቆ እቤቴ አገኘሁት፤” “ነገር ግን በደስታና በርኅራኄ እንደተቀበልነው ሲገነዘብና ራቱን አብልተን እኔው ቤት እንደሚያድር ሲገባው ሰውነቱ ሁሉ ተፍታቶ ገጽታው እጅግ በጣም ፈካ አለ።” ይላል ይሄ እንግሊዛዊ። ዳሩ ግን የዚህ የ’ጥቁር’ ልጅ በአንድ ጣራ ሥር እነሱ የሚተኙበት ፎቅ ላይ መተኛቱ ያላስደሰታቸው የሰር ኤድዋርድ ገረዶች እዚያው ቀዝቃዛ ማዕድ ቤት ውስጥ እንዲያድር ፈረዱበት። እታዘዘበት መሬት ላይ ከማንቀላፋቱ በፊት ግን መኝታው ጋ ቆሞ ለቅዱስ ጊዮርጊስ የሕሊና ፀሎት እንዳደረሰ ሁሉ ሲነግረን ስለዮሐንስ የሚተነተንልንን ታሪክ በኢትዮጵያዊ ዓይነ ልቦናችን እንድንገነዘበው ይረዳናል።

በማለዳ የተነሳው ዮሐንስ የተነፈሳቸው ቃላት፤ “ወደጌታዬ መሄድ እፈልጋለሁ” ሲሆን ካፕቴን ካሜሮን በ ‘ኮቬንት ጋርደን’ (Covent Garden ) አካባቢ ያረፈበትን የሆቴል ስም ልብ አድርጎ አጥንቶት ስለነበር “አሽከሬ ይዞት ወደ ሪችሞንድ የምድር ባቡር ጣቢያ እንዲሄድና እስከ ‘ወተርሉ የምድር ባቡር ጣቢያ’ የሚያጓጉዘውን ካርኔ እንዲያስቆርጥለት አዘዝኩ” ይለናል። ለጋሪ አንድ ሽልንግ፤ በ’ወተርሉ’ ድልድይ ላይ መሻገሪያ ደግሞ ሁለት ‘ፔንስ’ እንድተሰጠውም አብሮ ይነግረናል።   

ከመድረሻው የምድር ባቡር ጣቢያ እስከ በ‘ኮቬንት ጋርደን’ አካባቢ የሚገኘው የጌታው ሆቴል ድረስ ስለሚገጥመው የዋጋ ድርድር ካስረዱት በኋላ ከመሳፈሩ በፊት “ጌታዬን እሆቴሉ ያላገኘሁት እንደሆነ፤ እርስዎ (ሰር ኤድዋርድ) ቤት፤ ነጩ ቤት፤ ውጭ ጉዳይ ቤሮ ልምጣ ወይ ቢለኝ እሺ ስላልኩት ተደሰተ። ነገር ግን ሆቴል የሚባለውን ጽንሰ ሐሳብ ስለማይረዳው ጌታው ያለበትን ቦታ ለማስረዳት ጥቂት ተቸግረን ነበር።” ይለንና ደራሲው “በመጨረሻ ግን ዮሐንስ በገጽታው ላይ የማወቅ ፈገግታ ተላብሶ “ይሄ ነገር ፣ እቤት ውስጥ ይገቡና እራት-አልጋ ይላሉ በማግሥቱ ቁርስ ይላሉ ፤ ባለቤቶቹ አንድ ፓውንድ - ሁለት ፓውንድ ይላሉ?>> አለ።” በዚሁ ተሳፍሮ ወደሎንዶን አመራ።

ሰር ኤድዋርድ ከሰዐታት በኋላ የዮሐንስን መድረስ አለመድረስ ለማረጋገጥ ወደ ካሜሮን ማረፊያ ሆቴል ሄዶ  ከካሜሮን ጋር ሲያወጋ በደስታ የተሞላው የዮሐንስ ፊት ከጓዳው ብቅ አለ።

ፀሐፊው፣ ዮሐንስ እሸቴ ለካፕቴን ካሜሮን የላቀ አክብሮታዊ ስሜት እንደነበረው ከገለጸልን በኋላ ግን፤- ካፕቴኑ “ከጊዜያት በኋላ ዮሐንስን እየሰለቸው ሳይመጣ አልቀረም” ይላል። በዘለቄታ ምን እንደሚያደርገው ግራ የገባው የሚመስለው ካፕቴን ካሜሮን፤ ከግብጽ ገዝቶለት የነበረው ልብስ  ሲያልቅበት የተራ የአሽከር ልብስ አለበሰው። ዮሐንስ ይሄ ‘ውርደት’ እና እንደውም ይባስ ብሎ ካሜሮን መጫሚያውን እንዲጠርግለት ስላዘዘው ተናዶ “እኔ ወደ እንግሊዝ አገር የመጣሁት ጫማ ለመጥረግ አይዶለም።” ብሎት ነበር። የሚያስደንቀው ግን ካሜሮን የአሽከር ደውል ደውሎ ወይን-ጠጅ ወይም ሌላ ጠንከር ያለ መጠጥ እንዲያመጣለት ሲያዘው፤ መጠጥ የሚወደውን ጌታውን እንደሚጎዳው በማሰብ፤ የታዘዘውን ካዘጋጀ በኋላ እንባውን እየጠረገ ቡጢውን በመጠጡ ላይ ይቃጣና በረድ ሲልለት አምጥቶ ያቀርብለት ነበር።

አንድ በጎ አድራጊ ወዳጅ ወደካቶሊካዊ ማሠልጠኛ ቤት ለመላክ ዝግጁ እንደነበረ/ች እና ሌላ ወዳጅ ደግሞ ወደ መደበኛ ትምህርት ቤት ለማስገባት ፈቃደኛነታቸውን ገልጸው ቢሆንም የዮሐንስ የመጨረሻ ዕጣው ግን ወደአገሩ መላክ እንደነበር ሰር ኤድዋርድ በቁጭት ይተርካል። እንደሱ አስተያየት ዮሐንስ እንግሊዝ አገር ቆይቶና ትምህርቱን ተከታትሎ  ቢሆን ኖሮ የብሪታኒያ ወዳጅ ይሆን ነበር ይለናል።

እንግዲህ ካሜሮን ወደ ዠኔቭ ሲጓዝ ይሁን አስቀድሞ፤ ብቻውን ይሁን ከባልደረባ ጋር፤ በሰላም አገሩ ይግባ ወይም እንደወጣ ቀረ የሚሉትንና ሌሎችንም ጥያቄዎች የሰር ኤድዋርድ ሐተታ ባይገልጽልንም ይሄንን ታሪክ ከመቶ አርባ አምሥት ዓመታት በኋላ ለምንከታተል ኢትዮጵያውያን የዮሐንስ እሸቴ ታሪክ አርኪ ድምዳሜ ባለማግኘቱ ያስቆጨናል። ካሜሮንን ተከትሎ ዠኔቭ ሄዶ ነበር ቢለንም እንኳ፤ ጌታው  ግንቦት ፳፫ ቀን ፲፰፻፷፪ ዓ/ም ዠኔቭ ላይ ሲሞት የዮሐንስ መጨረሻው ምን ነበር? ማለታችን አይቀርም።

ደራሲው ዮሐንስ ከእንግሊዝ አገር ከሄደ በኋላ ባዝ ከተማ ላይ ስለዚሁ ኢትዮጵያዊ ታሪክ ያነሳውን ትንታኔ ታዳምጥ የነበረች አንዲት ሴት ወይዘሮ ይሄንን ልጅ ማስተማሪያ እንዲሆን የሃምሳ ፓውንድ የዓመት አበል ለመመደብ መወስኗን እንዳስታወቀችውና ዮሐንስም ወደአገሩ መመለሱን ሲነግራት በጣም እንዳዘነች ያጫውተናል።

ዮሐንስን ሳስታውሰው ይላል ሰር ኤድዋርድ “አንድ ቀን ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ውስጥ ከሌሎች መሪዎች ምስል መኻል የአበሻውን ንጉሥ ምስል ሲያይ “ወየው! ንጉሤ ዓፄ ቴዎድሮስ ነፃ መሪ መሆናቸውን እንደዚህ (በንግሊዞቹ) ታውቆላቸው እንደነበር ለማየት አብቅቷቸው ቢሞቱ ኖሮ አይቆጫቸውም ነበር።” ማለቱንም ነው በሚል ጥልቅ አበሻዊ ግንዛቤ ይደመድማል።



[1] The London Gazette; [p. 2719], Foreign Office, June 30, 1860


Monday 5 December 2011

‘እስከመቼ ፊትህን ታዞርብናለህ!’


ሰሞኑን በየድረ-ገጹ አበሾችን ወደየኮምፒውተር ሰሌዳቸው (ክትበ-ገበራቸው) እየገፋፋቸው ያለው በአገር ቤት ግብረ-ሰዶማውያን በኢትዮጵያ መንግሥት ድጋፍ ሊያደርጉት የተዘጋጁበት ስብሰባ ነው።

ስለዚህ ጉዳይ መጀመሪያ ያነበብኩት አዲስ-ሪፖርተር ባለፈው ዕሮብ ያወጣው ዘገባ ሲሆን፤ ይኼም የሃይማኖት አባቶች ጉዳዩን ለማውገዝ ያዘጋጁትን ውሳኔ ለጋዜጠኞች እንዳይስተላልፉ የጤና ጥበቃው ሚኒስትር ባልተገለጸ ምክንያትናዘዴ  እንዳስጣሏቸው ያበሰረው አንቀጹ ነው። ከዚኽ ቀጥሎ ያነበብኩት በዳንኤል ክብረት እይታዎች ላይእሳቱ ከሌለ ጢሱ አይታይምበሚል ርዕስ በዚያው ዕሮብ እለት ያሰፈረው መጣጥፍ ነው፡፡ ዳንኤል፣ ቅዳሜ ደግሞይህ ስም ክቡር ነው” በሚል ርዕስ ጠለቅ ያለ ዘገባ አስነበበን።

እነዚህ ትንተናዎች አያሌ አስተያየቶችን ስበዋል። አብዛኛዎቹ ተችዎች የዚህ ዜና አዎንታ ስሜታቸውን የቱን ያህል እንዳብሰለሰለውና እንዳሳረረው ከአጻጻፋቸው እንረዳለን። ግብረ-ሰዶማዊነት ከባህላችንም፣ ከሃይማኖታዊ እምነታችንም (በተለይ የኦርቶዶክስ ክርስትና) ጋራ የተጻረረ እና በጥብቅ የተከለከለ፤አስጸያፊ ድርጊት እንደሆነ እየደጋገሙ አስፍረውታል። አልፎ አልፎም ወቅታዊው የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግም ግብረ-ሰዶማዊነትን እንደሚከለክል ከነአንቀጹ በመጥቀስ ያስረዱንም አሉበት።

ዳንኤል “ኢትዮጵያ የሃይማኖት ሀገር ናት፡፡ ከ90 በመቶ በላይ የሆነው ሕዝቧ በእምነቱ ግብረ ሰዶምን ይቃወማል ብቻ ሳይሆን ይጸየፋል፡፡ የሀገሪቱ ሕጎችም ግብረ ሰዶማዊነትን በወንጀልነት ይፈርጃሉ፡፡ ከሕዝቡ እምነት ብቻ ሳይሆን ከባህሉ ጋርም የሚጣረስ ጉዳይ ነው፡፡” ብሎ እቅጩን ከነገረን በኋላ ከዚኽ ለጥቆም “ግብረሰዶማዊነትን ካልተቀበላችሁ፣ የግብረሰዶማውያንን መብት ካልደገፋችሁ አንረዳም እያሉ የሚያስፈራሩ ምዕራባውያን ኃያላን አሉ፡፡ ራሳችንን አጥተን የሚመጣ ርዳታ ለቀብር ማስፈጸሚያነት ብቻ የሚውል ነው፡፡ እናም እንዲቀርብን እንንገራቸው፡፡” በማለት የችግሩን መፍትሄ በከፊልም ቢሆን ሲጠቁም፤ ማንነታችንን እንወቅ፣ የሰፊውን ሕዝባችንን እምነትና ባህል የሚያረክሱ፣ የሚበክሉ፣ ባዕዳዊ ልምዶችን በስመ-ሥልጣኔ ወይም እርምጃ ለሣንቲም ብለን እየተቅበልን እራሳችንን አናዋርድ፣ አንግደል፣ አንቅበር እያለን ነው ያለው።

አንዱ ተች ደግሞ ምዕራገ ጸሎት፣ ዲቦ ቅድስት ድንግል ማርያም በምትባለው ገዳም ያሉ አባቶች በየዕለቱ በመላ አገሪቱ ውስጥ የተሰዋውን መስዋዕት የተጸለየውን ጸሎት እንደሚያሳርጉ ሲነግረን፤ እንዲህ ዓይነት ድርጊት የሚፈጸምባት ቅድስት ሃገር በተቃራኒው ርኩስ አስጸያፊ በሆነው በግብረ-ሰዶማዊነትም ስም አብራ መጠራት እንደሌለባት ሲይስታውሰን ሌላው ደግሞ (ስሙን እንኳን ያልነገረን ተቺ) የግል መብት ከሁሉም የበላይ እንደሆነና በግል ውሳኔ/ምርጫ ካቶሊክነት ወይም ኦርቶዶክሳዊነት ወይም እስልምና ወይም ሃይማኖተ-አልባ መሆን እንደምንችል ሁሉ፣ እንደግብረ-ሰዶማዊነትንም ያሉትን ተግባራት በግል መርጠን ማካሄድ መቻል መብታችን ነው ባይ ነው፡፡ ይኼኛው አስተያየት ሰጭ ታዲያ  ይፋ ከተደረጉት አስተያየቶች መኻል በጸረ ግብረ-ሰዶማውያን የተሰነዘሩት አስተያየቶች፣ ከሃይማኖት ወይም ከባህል ወይም ዝም ብሎ የመጥላት መንፈስ ውጭ ሌላ ምንም ዓይነት አስተያየት እንዳላየ ይተነትንና ሃይማኖታዊ የሆኑት ቅራኔዎች ለአማኞች ብቻ የሚሠሩ፤ ባህልን የተመረኮዙት ቅራኔዎች ደግሞ እንደማንኛውም ባህል ከጊዜ ሂደት ጋር እየተለወጡ መምጣት የማይቀርላቸው ናቸው ይለናል።

ታዲያ ይኼንን ሁሉ አንብቤ፤ እንደአብዛኛው ወገኔ እኔም በሀገሬ ላይ ያለኝ ተስፋ እየመነመነ፤ ውስጤ እየተቃጠለ፤ እንደኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ተከታይም፣ ወደፈጣሪ አምላኬም ‘እስከመቼ ፊትህን ታዞርብናለህ!’ ብዬ መጮኼም አልቀረም። የመንግሥት መገናኛ ብዙኃንስ በተለየ ስለዚህ የግብረ-ሰዶማውያን እንቅስቃሴም ኾነ ከፍተኛ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ ባለ-ሥልጣን የሃይማኖት አባቶች ላይ አደረጉ ስለተባለው ኢ-ዴሞክራሲያዊ የአፈና ተጽዕኖ ምን ብለው ይኾን ብዬ ብፈልግ፣ በሽምግልና በደከሙ ዓይኖቼ ስንፈት አልታይ ብለውኝ ካልኾነ በሰትቀር አንድም ነጥብ ላገኝ አልቻልኩም።

እኔን ታዲያ ወደዚህ ጽሑፍ የገፋፋኝ ይኼ ሁለተኛው አስተያየት ነው። በሃይማኖታዊ መሠረት የሚደነገግም ሆነ በዓለማዊ አስተዳደር በየጊዜው የሚተገበር ሕግ ሥር መሠረቱ የሚመነጨው ከተፈጥሮ ሕግጋትም መኾኑን መዘንጋት የለብንም። ለምሣሌ ያህል ይኼንን ጉዳይ የሚመለከተው የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ክፍል ሁለት ሲሆን ርዕሱ ‹‹ለተፈጥሮ ባሕርይ ተቃራኒ የሆነ የግብረ ሥጋ ግንኙነቶች›› ነው የሚለው። እንግዲህ በሰገላዊም ኾነ፤ ሃይማኖታዊ አገላለጽ ግብረ-ሰዶማዊነት “የተፈጥሮ ባሕርይ” ነው ብሎ  መሟገት ማለት በፍጡራን ውስጠ አካል፣ እንደ መተንፈስ፣ መመገብ እና የአካልን ብክነቶች የማስወገድ የመሳሰሉ ጠባያት ከንቁ-አዕምሮ ቁጥጥር ውጭ ለመራባት እና ራስን ከማጥፋት ለማዳን አብረውን የተፈጠሩ ግዴታዎች መሆናቸውን መካድ ነው። ሰው የተባለው ፍጡር ከተፈጥሮ ባሕርያቱ አንዱ ከተቃራኒ ፆታ ሰው ጋር ዘሩን የማርባት ግዴታውን ሟሟላት ከንቁ-አዕምሮ ውጭ የሚካሄድ ባሕርይ ነው። ይኼንን ደግሞ በግብረ-ሰዶማዊነት ማሟላት አይቻልም። አይ ግድ የለም! የግል መብት ስለሆነ ይፈቀድ ማለት ደግሞ ከተፈጥሮ ሕግ ጋር በመቃረን የሰው ልጅ ዘር ይጥፋ፤ እንዲጠፋም እናድርግ ማለት ነው።

በልጅነት ዘመኔ ባልንጀሮቼን የማታክትበት፤ እኔም ብሆን አሁን ከበሰልሁ በኋላ መለስ ብዬ ስገመግመው እኔውኑ የሚያሳፍረኝ አንድ ጠባይ ይዤ ነበረ። ደግነቱ እንደማንኛውም የልጅነት ጠባይ የጧት ጤዛ ሆኖ ነው የቀረው።  ለትንፋሻችን የምንጠቀመው ‘ኦክሲጂን’ የተባለው አየር በዓይናችን የማናየው፤ በእጃችን የማንዳስሰው ነገር ሆኖ፤ ዙሪያችንን ከቦ የሚገኝ እና ለመኖር የሚያስፈልጋቸው ፍጡራን ሁሉ የጋራ ንብረት ነው። በጎኑ ደግሞ ይኼን የጋራ ንብረት እኩል የመጠቀም መብት የያንዳንዱ ፍጡር ተፈጥሮአዊ መብት ሲሆን የባልንጀሮቼን ዓይን እስካልጠነቆልሁ ድረስ ዓይናቸው ስር ድረስ ጣቶቼን እያወናጨፍሁ በዓየር ላይ የመጠቀም መብቴን ካላሳመንኋችሁ እያልኩ አታክታቸው ነበረ። እውነትም የሰውን አካል እስካልነካን ድረስ (እንቅስቃሴያቸውን እየገታን እንኳ ቢሆንም) መብቴ በምንለው ነገር ሁሉ ላይ  እንዳሻን የመጠቀም መብት አለን ማለት በዚያ ባልበሰለ፣ ጨቅላ አዕምሮ አስተሳሰብ (በተለይም የጡንቻ ድጋፍ አለው ብለን ካመንን!) ማሳመን ይቻል ይሆናል። ነገር ግን የኔ አስተሳሰብ ጉድለቱ፤ መብት ማለት የሌላውን፤ ሃይማኖታዊም ይኹን ባህላዊ ወይም ተፈጥሮአዊ መብት እስካልነካ ድረስ ብቻ መሆኑን አለመገንዘብ ነበረ። እያንዳንዱ ፍጡር በሰውነቱ ዙሪያ እስከተወሰነ ርቀት ድረስ በዓይን የማይታይ፤ በእጅ የማይዳሰስ “የተፈጥሮ መንፈሱ (life-force) ወይም በባህላዊ ገለጻ፣ ውቃቢው የሚያስፈልገው ቦታ ሲወረርበት አይወድምም መብቱም እንደተነካበት ይቆጠራል።

እንግዲህ ለዚህ መጣጥፍ ያነሳሳኝ ሰው “የግል መብት ከሁሉም የበላይ ስለሆነ፣ እንደግብረ-ሰዶማዊነትንም ያሉትን ተግባራት በግል መርጠን ማካሄድ መቻል መብታችን ነው” ሲል ልክ እኔ በዚያ በርጥብ አስተሳሰቤ “ዓይንህን እስካልነካሁ ድረስ በዓየሩ ላይ ጣቶቼን ማወናጨፍ መብቴ ነው” እል እንደነበረው አይነት እጅግ የተዛባ እና ያልበሰለ አመለካከት ነው። በአሁኑ ጊዜ በየትኛውም ሕብረተ-ሰብ መገበያያ ተብሎ ጥቅም ላይ የሚገኘው በታተመ ወረቀት ወይም ከብረታ ብረት በተሠሩ ሣንቲሞች ነው። እኔም ሆንኩ ይኼ ወንድሜ ‘አይ እኔ መገበያየት የምፈልገው በአሞሌ ጨው ወይም አዝራር ነው” ማለት የግል መምረጥ መብታችን ቢሆንም ከሰው ፍጥረት ጋር እስካለን ድረስ የማይሠራ ባዶ-ቅል ኃሣብ ሆኖ እናገኘዋለን። ከኢትዮጵያ ሕብረተ-ሰብ ጋር ተቃራኒ የሆነ ተግባርንም በዚያ ሕብረተ-ሰብ መኻል የማካሄድ መብቴ ነው ማለትም እንደዚሁ ውዳሴ ከንቱ የኾነ አመለካከት ነው።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ከተፈጥሮ ግዴታዎች ተነስቶ በሃይማኖትም፤ በባህልም ሆነ በዘመናዊ አስተዳደር ሕግጋትን መሥርቶ በውዱ ሲተዳደርባቸው  እዚህ የደረሰ ሥልጡን ሕብረተ-ሰብ ነው። በሕብረተ-ሰብም ደረጃ ማሻሻልም ሆነ መለወጥ የሚያስፈልጋቸው ባህሎችም ሆኑ ልምዶች ቢኖሩትም ማንነቱን በማያዛባ እና ሁሉንም ወገን እኩል በሚጠቅም (ለዚያውም ተፈጥሮአዊ ግዴታን በማይቃረን መልኩ) እራሱ በራሱ ይለውጣቸዋል ወይም ያሻሽላቸዋል እንጂ ባዕድ ምዕራባውያን ባስቀመጡት መስፈርት ሊሆን አይችልም።

ይኼ እንግዲህ ‘የግል መብት’ በሚል አጠራር የምንመጻደቅባቸውን አዲስ ፈሊጦችን ሁሉ ያካትታል። አብሮም ልንረዳው የሚያስፈልገው ሌላው አዎንታ ደግሞ፤ በዴሞክራሲ ሥርዓት እንኳ ሕዝቡን የመምራትን ሥልጣን ጨብጠናል የሚሉት መሪዎችም ቢሆኑ የኢትዮጵያ ሕብረተ-ሰብ ተፈጥሮአዊንም ኾነ፤ እምነትን ወይም ባህልን ተመርኩዘው የተመሠረቱትን ሕግጋቱን በስሙ የማስከበር ሥልጣን እንጂ የመደምሰስ ወይም ሲደመሰስ ዝም ብሎ የማየት፤ የመለወጥ፤ የመጣስ ወይም የማስጣስ መብት የላቸውም። በዴሞክራሲ ሥርዓትም ሥልጣንን የጨበጡት ለኢትዮጵያውያን አገልግሎት እንጂ ለምዕራባውያን እያጎነበሱ ክብሩን ለማስገፈፍ እንዳልሆነ በፍጥነት ሊገነዘቡት ይገባቸዋል። አንዳንድ ነገሮች እጅግ አሰቃቂ፤ ነውር እና አይነኬ ናቸውና።

ኅዳር 25 ቀን 2004 ዓ/ም

Wednesday 4 May 2011

የ፸ ዓመት ነፃነት

        ሚያዝያ ፳፯ ቀን አባቶቻችንና እናቶቻችን አርበኞች ግፈኛውን የፋሺስት ኢጣልያ ሠራዊት ድል ያደረጉበት ማስታወሻ አድርገን እናከብረዋለን። በ፳፻፫ ዓመተ ምሕረት፣ ነገ ደግሞ ርዕሰ ከተማችንን በከፊል ተረክበን፣ ሰንደቅ ዓላማችን የተውለበለበበት ሰባኛው ዓመት ማስታወሻ ስለሆነ ለየት ባለ ሁኔታ ለማክበር እንሞክራለን። ከነኛ ጀግኖች አርበኞቻችን መኸል መቸም በጊዜው ብዛት አብዛኛዎቹ ተለይተውን፣ የቀሩት ጥቂት ናቸው።

በዚህ የመታሰቢያ ጽሑፍ  ከዚህ ዕለት ጋር የተያያዙ ሦስት ዐቢይ ነጥቦችን ለማንሳት እፈልጋለሁ። እነዚህም፦

ሀ)      የዚህን ዕለት ‘የነፃነት ቀን’ ወይም ‘የድል በዓል’ መባል ትክክለነቱን፤
ለ)      ለድሉ ወይም ለነፃነቱ ላደረሱን ጥቂት፣ ተራፊ አባቶች እና እናቶች አርበኞቻችን ምን ውለታ ተደርጎላቸዋል?
ሐ)      እኛ ኢትዮጵያውያን ለ ፸ ዓመታት በጃችን ይዘነው የቆየነውን ‘ነፃነት’ እንደምን ተጠቅመንበታል?

ሀ)     የድል በዓል ሚያዝያ ፳፯ ወይስ ኅዳር ፲፱ ?

ንጉሠ ነገሥቱ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በምዕራብ ኢትዮጵያ ኡም ኢድላ (ኦሜድላ) ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ከተከሉበት ጥር ፲፪ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ/ም ጀምሮ በጎጃም እንጃባራ፤ ቡርዬ፣ ደምበጫ፣ ደብረ ማርቆስ አድርገው በእንጦጦ በር አዲስ አበባ እስከገቡ ድረስ፤ በአርበኞቻችን ኃይልና በእንግሊዝ ጦር ኃይሎች እርዳታ የጣሊያንን ኃይል እየደመሰሱ በሚጓዙበት ወቅት በምሥራቅና በደቡብ ምሥራቅ ኢትዮጵያ የነበሩት አርበኞችና የእንግሊዝ ሠራዊት እንደዚሁ በጅጅጋ፣ ሐረር፣ ድሬዳዋ፣ አዋሽ፣ ናዝሬትና ሞጆ አድርገው፣ ከፊታቸው የሚያጋጥማቸውን የፋሺስት ኃይል እየደመሰሱ ወደርዕሰ ከተማዋ ይገሰግሱ ነበር።

ታዲያ ከነኚህ ሁለት ግንባሮች ቀድሞ ከተማዋን መጋቢት ፳፰ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም ከጣሊያኖች የተረከበው እንግሊዛዊው ጄነራል ዌዘሮል ነበር።[1]  ንጉሠ ነገሥቱ እና ተከታዮቻቸው ከአንድ ወር በኋላ፣ ሚያዝያ ፳፯ ቀን አዲስ አበባን ተረከቡ።

በዚህ ጊዜ በደቡብ-ምዕራብ ኢትዮጵያ፤ ጅማ እስከ ግንቦት ፳፱ ድረስ በሰሜን ኢትዮጵያ ደግሞ ጎንደር እስከ ኅዳር ፲፱ ቀን ፲፱፻፴፬ ዓመተ ምሕረት ድረስ በጣሊያኖች እጅ ነበሩ።

እንግዲህ እንደምንገነዘበው 'ድል ቀን' ሚያዝያ  ፳፯ ቀን የሆነበት ዋናው እና ብቸኛው ምክንያት ንጉሠ ነገሥቱ አዲስ አበባ የገቡበት ዕለት ስለሆነ እንጂ መላዋ አገር ከፋሺስት ቀንበር የተላቀቀችበት ሆኖ አይደለም። ትክክለኛ ሆኖ መከበር ያለበት የጣሊያን ሠራዊት ለመጨረሻ እና ለዘለዓለም ሰንደቅ ዓላማውን ከኢትዮጵያ ምድር ያወረደበት እና ያለምንም ጥርጣሬ መሸነፉን አምኖ ጎንደር ላይ እጁን የሰጠበት ዕለት ኅዳር ፲፱ ቀን  ፲፱፻፴፬ ዓመተ ምሕረት መሆን ይገባዋል። 

ያለበለዚያማ በዚህ በመጨረሻው ግንባር ተሰማርተው ሲጋደሉ የቆዩትን አባቶቻችንን መስዋእትነት መዘንጋት፣ መደምሰስ ይሆንብናል። የእነ  ደጃዝማች ኪዳኔ ወልደመድኅን ደጃዝማች ሀብተ ሥላሴ በላይነህ ደጃዝማች በዛብህ በለው፣ ደጃዝማች ካሣ መሸሻ፣  ደጃዝማች ከበደ ወንድማገኝ፣ ፊታውራሪ ከበደ ካሣ፣ እና የሌሎችም ብዙ አባቶቻችን አፅም ይፋረደናል። ሌሎቹ አርበኞች፣ ስደተኞች ከአምሥት ዓመታት በኋላ ወደየዘመድ አዝማዳቸው፣ ወደየትውልድ አገራቸው ሲመለሱ፣ እነኚህ ግን ትጥቃቸውን ሳያወልቁ፣ ቅማል የወረረውን ጎፈሬያቸውን ሳይቆረጡ ወደሰሜን ዘመቻ ተሰማሩ። የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ከሚያዝያ ፴፫ እስከ ኅዳር ፴፬ ያሉትን ሰባት ወራት የደመሰሰባቸው ይበቃል።

'ድል በዓል' ዕለት መከበር ያለበት ሰንደቅ ዓላማ የተተከለበት ዕለት ከሆነ፣ እንግዲያውስ ኡም ኢድላ (ኦሜድላ) ላይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የትተከለበት ጥር ፲፪  ቀን ይከበራ! አይ፣ አዲስ አበባ ከፋሺስት ኢጣልያ እጅ የተፈለቀቀችበት ዕለት መሆን አለበት የተባለ እንደሆነ ደግሞ፣ እንግሊዛዊው ማጆር ጄኔራል ዌዘሮል ዋና ከተማዋን የተረከበበት መጋቢት ፳፰  ቀን ይሁና! የዚህኛው ቀን ችግር ግን ዌዘሮል ያውለበለበው የብሪታኒያን ሰንደቅ ዓላማ መሆኑ ነው።

እነዚህ ሁሉ የተለያዩ ቀናት እንድ ሚያዝያ ፳፯  'ድል' የሚለውን ቃል ሙሉ በሙሉ አርኪ በሆነ መልድ አያስተጋቡም። ኅዳር ፲፱ ቀን ግን የፋሺስትን ኃይል ከመላዋ ኢትዮጵያ ክልል አሽቀንጥረን አስውጥተን፣ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ዓላማችን በመላው አገራችን የተውለበለበበት፣ ራሳችንን በራሳችን የማስተዳደር መብታችን የተከብርበት ዕለት [የሰባት ዓመቱን የእንግሊዞችን ጣልቃ ገብነት ወደጎን ትተነው] በመሆኑ እውነተኛው "የድል ዕለት" ያደርገዋል።
ለ)     አርበኞች አባቶቻችን እና እናቶቻችን ስለስድስት ዓመት ተጋድሏቸው ምን ውለታ አገኙ?
        
ጠላት ኢትዮጵያን በወረረ ጊዜ አብዛኛዎቹ ተከላካይ ወገኖቻችን ዕድሜያቸው ከአሥራ ስምንት ዓመት እስከ ሃያ አንድ ዓመት ብቻ የነበሩ ወጣቶች ናቸው። አብዛኞቹ፣ የጦር መሪዎቻቸው፣ መኳንንቱ፣ መሣፍንቱ  ከነአካቴውም ንጉሠ ነገሥቱም ሳይቀሩ አጋፍጠዋቸው አገር ጥለው እግሬ አውጪኝ ሲበሩ፤ ሞትም እንኳ ቢመጣ ለጠላት አንገዛም ብለውት፤። ረሀብ ሲቆላቸው፣ ቅማል ደማቸውን ሲመጠምጥ፣ የመርዙ ጋዝ፣ የቦምባርዱ፣ የጥይቱ የተቅማጡ፣ እረ ምኑ-ቅጡ 

መንፈሰ ጠንካራ፣ አልበገር ባይ ባይሆኑማ ኖሮ እነሙሴ ቀስተኛን የመሰሉ ሰላዮች መኻላቸው እየገቡ፤ ‘ንጉሡ ጥሏት ለሄደው አገር ስለምን ትጉላላላችሁ? ኑ ግቡ፤ የኢጣልያ መንግሥት ይሾማችኋል፣ ይሸልማችኋል’ እያሉ አገራቸውን ሊያስከዷችእው ሞክረው አልነበረም?  ያ ትውልድ ግን ‘ለጥቅሜ ብዬ ውድ አገሬን፣ አለኝታዬን፣ መኩሪያዬን አሳልፌ አልሰጥም። ለነፃነቴ ብሞትም ክብሬ የዘለዓለም ነው።’ በሚል ጥብቅ እምነታቸው ተሰቃዩ፣ አጥንታቸውን በየሸንተረሩ ከሰከሱ፣ ደማቸው በየ ሸለቆው ፈሰሰ፤ እንደጥብቅነታቸው እንደ እምነታቸው ታዲያ ያንን መራራ ጠላት ከወሰን ድንበራቸው ለማባረር በቁ።

የዓፄ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት በነኚህ ኢትዮጵያውያን ደም ተመልሶ ሥልጣኑን ሲጨብጥ፣ እንደባለውለታ መንከባከብ፣ መሾም መሸለም፣ ማክበር ማስከበር ሲኖርበት፤ ከነአካቴው ውለታ ተቀባይነታቸው ቀርቶ እንደውለት መላሽ የትም ወድቀው እንዲቀሩ፣ ስማቸው እንዲጠፋ፣ ሥራ ስጡን ብለው በ’ደጅ ጥናት’ እንዲማቅቁ የሚጥር ሥርዓት ሆነባቸው። በስማቸው የተሠራውን የአራት ኪሎውን ሕንፃ እንኳን ለማስፈቀድ የነበረባቸውን እንግልት ይሄ ጸሐፊ በቅርብ ታዝቦታል። የኢትዮጵያ መንግሥት እነኚህን ባለውለታዎች፣ ሲሆን እስከ ጡረታ ዕድሜያቸው አገራቸውን እንዲያገለግሉ፤ ቢያንስ እንኳ ለዚያ ውለታቸው ክብራቸውን ጠብቆ በእንክብካቤ መጦር ሲገባው ነፍስ አውጪኝ የሸሹትን ስደተኞች ሲሾም ሲሸልም፣ እነኚህን ግን ከኢትዮጵያ ማዕድ ከልክሏቸው ኖረ።

በደርግ ዘመናት ደግሞ ጭርሱንም በትምህርት ቤት እንኳ ከአብዮቱ በፊት የነበረውን ታሪክ ወጣቱ እንዳይማረው ተከለከለ። ትንሽ መተዳደሪያ መሬት የነበራቸው ተነጠቁ። ወገን ለሌላቸው አርበኞች መርጃ ተብሎ የተሠራው የአራት ኪሎ ሕንፃቸው ሳይቀር ተወረሰ። መጦር የነበረባቸው የነፃነታችን ባለቤቶች እየለመኑ መኖር ግዴታ ሆነባቸው።[2]

ባለፉት ሃያ ዓመታትማ ብሶበታል። አንደኛ ቁጥራቸውም እያደር እየመነመነ ነው። ከሁሉም በላይ ግን የአሁኑም መንግሥት የነኚህን ባልውለታዎች ታሪክ ማንቋሸሽና ማጣጠል እንጂ ክብር መስጠትን የማያውቅ፤ ዘመኑ እንኳን ለሰማንያ፣ ዘጠና ዓመት አዛውንት ቀርቶ እየሠራ የሚበላው ወጣት ትውልድ ሊቋቋመው የማይችለው፣ ሽማግሌ ማክበር፣ መርዳት የነበረው የባህላችን ምሰሶ በሥልጣኔ፣ እድገትና እርምጃ ስም ሌት ተቀን በመጥረቢያ ስለት እንደሚከተከት ግንድ ሊወድቅ ምንም ያልቀረው ሆኗል። ታዲያ ለእነኚህ ባለውለታችን አዛውንት ምን ተስፋ አላቸው?

ሐ) የ፸ ዓመት ነፃነታችንን ምን ሠርተንበታል?
ከ፴፫ቱ ድል ጋር አብረው የገቡት እንግሊዞች ምሥጢራዊ ዓላማቸው ፋሺስት ኢጣልያን በቅኝ ገዥነት መተካት ኖሮ በስም የንግሊዝ ቅኝ ግዛት አንባል እንጂ በተግባር ግን እንደመዥገር ተጣብቀውብን ደማችንን ሲመጡ የኖሩባቸውን ሰባት ዓመታት ትተን በቀሩት ፷፫ ዓመታት ላይ ብናተኵር፤ ይሄንን ጥያቄ እንዴት ነው የምንመልሰው?
የዘውዱ ሥርዓት ከስደት እንደተመለሰ ሥልጣኑን በማጠናከር፣ ፈላጭ፣ ቆራጭ ሆኖ ፣የአምሥቱን ዓመታት ፍዳ ረስቶ/አስረስቶ ለሃያ ዓመታት ከገዛ በኋላ፤ የወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ቢደርግበትም የጭቆና ባሕሪውን አባባሰው እንጂ ለሕዝቡ ንቃት እና መሻሻል ምንም ይሄ ነው የሚባል ለውጥ አላመጣለትም። የዚያ የታኅሣሡ ሙከራ ግን በሕዝቡ ልቦና ላይ የጫረው የለውጥ እሳት ከ ፲፫ ዓመታት በኋላ ተፋፍሞ አሽቀንጥሮ ጣለው።
ተከታዩ አብዮት፣ ሕዝቡ እንደተመኘው፣ እንዳለመው የዴሞክራሲያ ውጤትን ሳይሆን የተጎናጸፈው፤ ጭርሹንም ከመቶ ዓመት በላይ ወደኋላ የገፈተረው ሥርዓት ሆነ። የሕዝብን ሉዐላዊነት፣ የሕግን የበላይነት፣ እኩልነትን፣ በኢትዮጵያዊነት ታሪክ ላይ የተመሠረተ ሥልጣኔን የሚሻ ሕዝብ ከነአካቴው ከጨካኞች የባሰ ጨካኝ፤ ከዲያብሎስ የበለጠ አረመኔ የአምባ ገነን ተገዢ አደረገው። በዲሞክራሲያ ፋንታ ለስድብ፣ ለውርደት፣ ለሞት ተዳረገ። የኢትዮጵያዊነት ወኔውን ተሰለበ።
ደሞ ያንን አሰቃቂ እና ፍሬ ቢስ ዘመን ከ፲፯ ዓመታት በኋላ ተገላገልኩ ሲል፤ ለባሰ ሥርዓት ከተዳረገ እነሆ ሀያ ዓመቱ ሆነ። ተለያይቶ የማያቀውን አንድ ሕዝብ በዘር አከፋፍሎ፣ አገርን በጉልበት ለመንጠቅ ለብዙ መቶ ዓመታት ሞክረው ያቃታቸውን ባዕዳውያንን በይፋ እየቆረሰ ‘ኑ ውሰዱልኝ’የሚል፣ የበላዩ ሊሆን የሚገባውን ሰፊውን የኢትዮጵያ ሕዝብ መብቱን ገፎ የሚገዛ የጉድ ጉድ፣ መዓት አናታችን ላይ ተመቻችቶ ቁጭ እንዲል ፈቀድንለት።
ዳግማዊ ምኒልክ የዛሬ መቶ ዓመት፣ ዕለተ ሞታቸው ሲቃረብ፤ ሕዝባቸውን እንዲህ ብለው መክረው ነበር፦

«እናንተ አንድ ልብ ከሆናችሁ በምቀኝነት እርስ በርሳችሁ ተዋግታችሁ ካላለቃችሁ በቀር ኢትዮጵያን አገራችንን ለሌላ ለባዕድ አትሰጧትም፤ ክፉም ነገር አገራችንን አያገኛትም። ነፋስ እንዳይገባባችሁ አገራችሁን በያላችሁበት በርትታችሁ ጠብቁ፤ ወንድሜ ወንድሜ እየተባባላችሁ ተደጋገፉ፤ የኢትዮጵያን ጠላት ተጋግዛችሁ ተድንበር መልሱ። የኢትዮጵያ ጠላት ባንዱ ወገን ትቶ ባንድ ወገን ቢሄድና ድንበር ቢገፋ፤ በኔ ወገን ታልመጣ ምን ቸገረኝ ብላችሁ ዝም አትበሉ፤ ያ ጠላት በመጣበት በኩል ኁላችሁም ሄዳችሁ አንድነት ተጋግዛችሁ ጠላታችሁን መልሱ እስከ እየቤታችሁ እስኪመጣ ዝም ብላችሁ አትቆዩ»
 ይሄ ቃላቸው በታሪክ አውሎ ነፋስ ተምዠግዥጎ እኛም ዦሮ ሲገባ፣ መልእክቱ ለዘመናቸው ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለኛም፤ ለመጪውም ትውልድ እንደሆነ እንገነዘባለን። በዛሬው የመከፋፈል፣ የዘረኛነት እና መንፈሰ ደካማ ሥርዓት ግን ምኒልክ ከነአካቴው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት ተብለው ተወነጀሉ።
በበኩሌ ያንን ሁሉ መሥዋዕትነት፣ ያንን ሁሉ ተጋድሎ አባክነነዋል እላለሁ እንጂ የ፸ ዓመት ነፃነታችንን በአግባቡ ተጠቅመንበትም ለወደፊቱም ትውልድ ቋሚ ነገር ለማሸጋገር በቅተናል አልልም።

የሎንዶኑ ቡልጌ ነኝ
[ሚያዝያ ፳፮ ቀን ፳፻፫ ዓ/ም]





[1] The Abyssinian Campaigns, Issued for the War Office by the Ministry of Information (1942)